#መሰረታዊ_የቤተክርስቲያን_ክርስቲያን_ትምህርት / #የተለያዩ_ተከታታይ_ትምህርት ' #ስንክሳር_የቅዱሳን_ገድል_በየዕለቱ ! #ስዕለ_አድህኖ ! #ምስባክ #የየበአላቱ_ዋዜማና_ሥርተ_ማህሌት #መዝሙር #ግጥም #ለመናፍቃን_ጥያቄ_መልስ እና የተለያዩ የቤተክርስቲያን ዶግማና ቀኖና የጠበቁ ሌሎች መንፈሳዊ ጽሁፎች ይለቀቁበታል Administration @zearsema_dn
ከትንሳኤ እሁድ በኋላ ያሉ ዕለታት ስያሜ፡-
#ሰኞ
#ማዕዶት_ይባላል፡- ማዕዶት ማለት መሻገር፣ ማለፍ ማለት ነው፡፡ በዚህ ዕለት በፋሲካችን በክርስቶስ ትንሣኤ ከድቅድቅ ጨለማ ወደ ሚደነቅ ብርሃን፣ ከሞት ወደ ሕይወት፣ ከሲኦል ወደ ገነት፣ ከሃሳር ወደ ክብር መሻገራችንን እናስባለን፡፡
#ማክሰኞ
#ቶማስ_ይባላል፡- በዚህ ዕለት ቶማስ ጌታን አይቶ ማመኑ፤ ጌታዬና አምላኬ ብሎ መመስከሩ ይዘከራል፡፡ ዮሐ. 20፡27-29
#ረቡዕ
#አልአዛር_ይባላል፡- በዚህ ዕለት ትንሣኤና ሕይወት የሆነው ጌታ ኢየሱስ አልአዛርን ከሞት እንዳስነሳው እናስባለን፡፡ ክርስቶስ የሞትን ስልጣን የሻረ የሕይወት ራስ፤ የመቃብርን ሥርዓት ያጠፋ ትንሣኤ፡ በድልም ያረገ ንጉሥ መሆኑን እንመሰክራለን፡፡
#ሐሙስ
#አዳም_ሐሙስ_ይባላል፡- በዚህ ዕለት ለአዳም የተሰጠው ተስፋ እና የተገባለት ኪዳን እንደተፈጸመ አዳምና ልጆቹ ነጻ እንደወጣን እናስባለን፡፡
#አርብ
#ቅድስት+ቤተክርስቲያን_ይባላል፡- በዚህ ዕለት ቤተክርስቲያን በክርስቶስ ሞትና ትንሣኤ ስለመመስረቷ ይሰበካል፡፡ ክርስቶስ ስለ እርሷ ራሱን አሳልፎ ሰጥቶ ቤዛ ሆኖ በደሙ አንጽቶ በትንሣኤው ድል ሰጥቶ እንዳከበራት ይነገራል፡፡ ቤተክርስቲያን ስንል ሕንፃውን ሳይሆን አማኞችን ነው፤ ክርስቶስ ለሕንፃ አልሞተምና፡፡
#ቅዳሜ
ቅዱሳት_አንስት_ይባላል፡- በዚህ ዕለት ቅዱሳት አንስት የክርስቶስን አካል ሽቶ ለመቀባት ጨለማ አቋርጠው ወደ መቃብር መምጣታቸውና ትንሣኤውንም ቀድመው ማየታቸው ይሰበካል፡፡
#እሁድ
#ዳግም_ትንሳኤ_ይባላል፡- በዚህ ዕለት ክርስቶስ ለሦስተኛ ጊዜ ለደቀመዛሙርቱ ተገልጦ ሰላምን መስበኩ እና ሥልጣንን መስጠቱ ይሰበካል፡፡
ፋሲካ አልባ ፋሲካ
ለሃምሳ ቀናት ጾመን ደርሰን ከኀዘን አጽናፍ
በስግደት በለቅሶ ከርመን ቆመን ከሰቆቃ ጫፍ
እንደ ሐዲስ ኪዳንናዊ ሰው ከርመን ወንጌል ስናጠና
እግዚኦ መሐረነ ጌታ ብለን ጮኸን ሆሳዕና
ሕማምህ መከራህ አልፎ ትንሣኤህ ሲመጣ ፋሲካ
ልክ እንደ ኦሪት ሰው ሆንን ሮጥን እንስሳ ፍለጋ
እንደ ክርስቲያኖች ወግ ሥጋህንበልተን እንደመዳን
በግና ዶሮ ልናሳድድ ሔድን ወደ ብሉይ ኪዳን
ስንት ሰዓት ልቁረብ ማለት ትተን የእርዱ ነገር አስጨነቀን
ከትንሣኤህ ዕለት ቆመን የልብ ትንሣኤ ራቀን
የመቃብርህን ውጪ ቆመው ደጅ ደጁን ከጠበቁ
ሕያው ጌታ መሆንህን ክብርህን ጭራሽ ካላወቁ
ከሮማውያን ወታደሮች በምን ተለየን እኛ
ሥጋህን ተቀብለን ካልሆነን የነፍስ መዳኛ
ከቶ እንዴት ይከበራል ወደ አንተ ሳይቀርቡ ትንሣኤ?
ለእኛ አልነበረም ወይ ያ ዕንባ ያ ሁሉ ኤሎሄ ኤሎሄ
የከበረው ሥጋህ ዛሬ በእኛ ውስጥ ካልተቀበረ
ምኑን ትንሣኤ ተበሰረ ምኑን ፋሲካ ተከበረ?
ይቅር በለን ጌታችን ሆይ በዶሮ ሥጋ ላከበርንህ
የሥጋችንን ስናሳድድ በትንሣኤህ ቀን ለቀበርንህ
በሞትህ ሙት ያስነሣህ ሆይ እኛንም አስነሣን ዛሬ
ደርቀን አንቅር በኃጢአት አድርገን የትንሣኤህ ፍሬ
ዲያቆን ሄኖክ ኃይሌ
ቀዳም ስዑር
ሚያዝያ 2016 ዓ.ም.
/channel/dnhayilemikael🌿
የሕፅበተ እግር ስነ ሥርዓት በመንበረ ፓትርያርክ ቅድስተ ቅዱሳን ማርያምገዳም ቅዱስ ፓትርያርኩ በተገኙበት ተከናወነ !
ሚያዝያ 24 ቀን 2016 ዓ.ም
ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ቀዳማዊ ፓትርያርክ ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀጳጳስ ዘአክሱም ወእጨጌ ዘመንበረ ተክሃይማኖት በመንበረ ፓትርያርክ ቅድስተ ቅዱሳን ማርያም ገዳም በመገኘት የሕፅበተ እግር ስነ ሥርዓት አከናውነዋል።
ዕለተ ሐሙስ እንደሚታወቀው ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በፍጹም ትህትና የደቀ መዛሙርቱን እግር ያጠበበት ከሐዋርያት ጋር ግብር የገባበትና የክርስትና ሕይወት ማኅተም የሆነውን ምስጢረ ቁርባን ያከናወነበት ዕለት ነው።
ስነ ሥርዓቱም ብፁዓን አበው ሊቃነ ጳጳሳት ፣ ቆሞሳት ፣ ካህናት እና በርካታ ምዕመናን በተገኙበት ሃይማኖታዊ ይዘቱን በጠበቀ መልኩ ተከናውኗል ።
ምንጭ ተዋሕዶ ሚዲያ
/channel/dnhayilemikael🌿
🌿🌿🌿🌿🌿🌿🌿🌿🌿🌿🌿✍#ሆሳዕና_ማለት_ምን_ማለት_ነው ??
🌿🌿🌿🌿🌿🌿🌿🌿🌿🌿🌿
#በሆሳዕና_ለምን_ቀለበት_እናስራለን ?
#በሆሳዕና_ጌታችን_ለምን_በአህያ_ላይ_ተቀመጠ
#በሆሳዕና_ለምን_ዘንባባ_አነጠፉ ?
................................................................
እና ሌሎች በደንብ ይነበብ ሼር!
=> ሆሳዕና ማለት ምን ማለት ነው??
ሆሳዕና ማለት፦ የዕብራይስጥ ቃል ሲሆን ትርጉሙ ‹‹እባክህ አሁን አድን አሁን ባርከን›› ማለት ነው፡፡በሰሙነ ሕማማት ጸሎተ ፍትሃት ጸሎተ አስተስርዮ ስለማይፈጸም ጸሎተ ፍትሃትና አስተስርዮ
የሚደረገው በዚሁ ዕለት ነው::
🌿🌿🌿🌿🌿🌿🌿🌿🌿🌿🌿🌿
=> በሆሣዕና ዕለት በእጃችን እደ ቀለበት ማሰራችን የምን ምሳሌ ነው??
1.ጌታ ለአዳም የሰጠው ቃል ኪዳን ለማስታወስ፡-ከልጅ ልጅህ ተወልጄ አድነሃለሁ ያለውን የተስፋ ቃል ለማስታወስ፡፡
2.ጌታ ለእመቤታችን የገባላትን ቃል ኪዳን ተምሳሌት ነው።
3.ጌታ ለእስራኤላውያን የሰጣቸው ቃል ኪዳን ተምሳሌት ነው።
4.ጌታ ለአዳም ከሰይጣን ግዛት ነጻ እንዳወጣው ሁሉ እኛም ከሰይጣን ግዛት ከመከራ ሥጋ ከመከራ ነፍስ ከክፋት ከኃጢአት አውጣን ማረን ለንስኃ ሞት አብቃን ከቤትህ አትለየን እንደ ቸርነትህ ይቅር በለን ስንል ለጌታ ዳግም ላናጠፋ ቃል የምንገባበት ነው፡፡
🌿🌿🌿🌿🌿🌿🌿🌿🌿🌿🌿🌿
=> ጌታችን በዕለተ ሆሳዕና ለምን በፈረስ ላይ አልተቀመጠም??
ትንቢቱንና ምሳሌውን ለመፈጸም ነው፡፡ "
አንቺ የጽዮን ልጅ ሆይ፥ እጅግ ደስ ይበልሽ ፤ አንቺ የኢየሩሳሌም ልጅ ሆይ፥ እልል በዪ፤ እነሆ፥ ንጉሥሽ ጻድቅና አዳኝ ነው፤ ትሑትም ሆኖ በአህያም፥ በአህያይቱ
ግልገል በውርጫይቱ ላይ ተቀምጦ ወደ አንቺ ይመጣል።(ትንቢተ ዘካርያስ 9:9)
=> በአህያ መቀመጡ፦
🌿🌿🌿🌿🌿🌿🌿🌿🌿🌿🌿
•ትህትናን ለማስተማር
•የሰላም ዘመን ነው ሲል
•ለፈለጉኝ ሁሉ የቅርብ አምላክ ነኝ ሲል በንጽህና በየዋህነት ለሚኖሩ ምዕመናን አድሬባቸው እኖራለሁ ሲል፡፡
•አህያዎች ትሁታን ናቸው ረጋ ብለው ነው
የሚሄዱት፤በቀላሉ ትወጣበታለህ፤በቀላሉ
ትይዘዋለህ፤እንደፈለክም ታዝዋለህ።
=> ጌታችን ወደ ኢየሩሳሌም ሲገባ ዘንባባ የመነጠፉ ሚስጢር የምን ምሳሌ ነው???
1.ዘንባባ፡- ይስሃቅ በተወለደ ጊዜ ደስ ብሎት አብርሃምን ዘንባባ ይዞ እግዚአብሔር አመስግነዋል፡፡
2.ዘንባባ ደርቆ እንደገና ሂይወት ይዘራል፡- የደረቀ የምታለመልም አምላክ ነህ ሲሉ ነው፡፡
3.ዘንባባ የሰላም ምልክት ነው፡- የሰላም አምላክ ነህ ሲሉ ነው።
4.ዘንባባ የደስታ መግለጫ ነው፡- አንተ ደስ የምታሰኝ ሃዘናችንም የምታርቅልን አምላክ ነህ ሲሉ ነው፡፡
5.ዘንባባ እሾሃማ ነው፡- አንተ ህያው አሸናፊ አምላክ ነህ ሲሉ ነው፡፡
6.ዘንባባ እሳት አይበላውም ለብልቦ ይተወዋል እንጂ፡፡ ጌታም አንተ ባህሪህን የማይመረመር ነው ሲሉ ነው፡፡
ህዝቡ ከልብሳቸው ሌላ ስንት አይነት ቅጠንል አነጠፉለት ምን ምን??
🌿🌿🌿🌿🌿🌿🌿🌿🌿🌿🌿🌿
=> ልብሳቸውን ማንጠፋቸው፡-
ለክብሩ መግለጫ ነው፡፡
ሌሎችም ሦስት አይነት ቅጠል አነጠፉለት ዘንባባ፤የቴመር ዛፍ፤የወይራ ዛፍ አነጠፉለት፡፡
=> ትልቅዋ አህያ በምን ትመሳለለች ውርጭለዋስ???
ትልቅዋ አህያ የኦሪት ምሳሌ ነው።
1.ትልቅዋ አህያ ሸክም የለመደች ናት ህገ ኦሪትም የተለመደች ህግ ናትና፡፡
2.የእስራኤል ምሳሌ ነው፡-ትልቅዋ አህያ ሸክም እንደለመደች ሁሉ እስራኤልም ህግ ለመፈጸም በህግ ለመራመድ የለመዱ ናቸው፡፡
3.የአዳም ምሳሌ ነው፡- አዳም ሸክም የበዛበት ነበርና።
🌿🌿🌿🌿🌿🌿🌿🌿🌿🌿🌿
ውርጭላዋ
1.በህገ ወንጌል ትመሰላለች፡-ምክንያቱም ወንጌል ኢየሱስ ክርስቶስ የመሰረታት የሰራት አዲስዋ ህግ ናትና፡፡
2.በአህዛብ ትመሰላለች፡-ትንሽዋ አህያ ሸክም የለመደች አይደለችም እንዲሁም አህዛብም ህግህን የመቀበል የመቀበል የለመደ አይደሉም፡፡ ለህግህ አዲስ ናቸውና፡፡
3.የእመቤታችን ምሳሌ ናት፡- የዓለም ሸክም አቅልላለችና በእመቤታችን ትመሰለላለች፡፡ እመቤታችን ድህነተ ምክንያታችን ጌታን የተሸከመች ንጽህት እንከን የሌላት እናት ናትና፡፡
መልካም በአል
🌿🌿🌿🌿🌿🌿🌿🌿🌿🌿
።።።።ወስበሐት_ለእግዚአብሔር ።።።።
።።።።። ወለወላዲቱ_ድንግል ።።።።።
።።።።። ወለመስቀሉ_ክቡር ።።።።።
🌿/channel/dnhayilemikael🌿
ሮሜ 12
¯¯¯¯¯¯¯¯¯¯
⁹ ፍቅራችሁ ያለ ግብዝነት ይሁን። ክፉውን ነገር ተጸየፉት፤ ከበጎ ነገር ጋር ተባበሩ፤
¹⁰ በወንድማማች መዋደድ እርስ በርሳችሁ ተዋደዱ፤ እርስ በርሳችሁ ተከባበሩ፤
¹¹ ለሥራ ከመትጋት አትለግሙ፤ በመንፈስ የምትቃጠሉ ሁኑ፤ ለጌታ ተገዙ፤
¹² በተስፋ ደስ ይበላችሁ፤ በመከራ ታገሡ፤ በጸሎት ጽኑ፤
¹³ ቅዱሳንን በሚያስፈልጋቸው እርዱ፤ እንግዶችን ለመቀበል ትጉ።
¹⁴ የሚያሳድዱአችሁን መርቁ፥ መርቁ እንጂ አትርገሙ።
¹⁵ ደስ ከሚላቸው ጋር ደስ ይበላችሁ፥ ከሚያለቅሱም ጋር አልቅሱ።
¹⁶ እርስ በርሳችሁ በአንድ አሳብ ተስማሙ፤ የትዕቢትን ነገር አታስቡ፥ ነገር ግን የትሕትናን ነገር ለመሥራት ትጉ። ልባሞች የሆናችሁ አይምሰላችሁ።
¹⁷ ለማንም ስለ ክፉ ፈንታ ክፉን አትመልሱ፤ በሰው ሁሉ ፊት መልካም የሆነውን አስቡ።
¹⁸ ቢቻላችሁስ በእናንተ በኩል ከሰው ሁሉ ጋር በሰላም ኑሩ።
¹⁹ ተወዳጆች ሆይ፥ ራሳችሁ አትበቀሉ፥ ለቍጣው ፈንታ ስጡ እንጂ፤ በቀል የእኔ ነው፥ እኔ ብድራቱን እመልሳለሁ ይላል ጌታ ተብሎ ተጽፎአልና።
²⁰ ጠላትህ ግን ቢራብ አብላው፤ ቢጠማ አጠጣው፤ ይህን በማድረግህ በራሱ ላይ የእሳት ፍም ትከምራለህና።
²¹ ክፉውን በመልካም አሸንፍ እንጂ በክፉ አትሸነፍ።
‹‹ጌታውን ያስደሰተው አገልጋይ ታማኝና ቸር አገልጋይ ነው››
ቅዱስ ያሬድ
💠ከማንም አስቀድሞ አገልግሎት ለአምላካችን እግዚአብሔር ይገባል፤ በጥንተ ተፈጥሮ በመጀመሪያው ቀን የተፈጠሩት መላእክት ፈጣሪያቸውን ዘወትር ያለማቋረጥ ‹‹ቅዱስ ቅዱስ ቅዱስ›› እያሉ እንደሚያመሰግኑት ሊቁ ቅዱስ ኤጲፋንዮስ በመጽሐፈ አክሲማሮስ ገልጾልናል፡፡ (አክሲማሮስ ዘእሑድ) በዕለተ ዓርብ ሰው ሲፈጠር እንደ መላእክቱ የፈጠረውን ጌታውን እንዲያመሰግን፣ እንዲያገለግል እንዲሁም ስሙን እንዲቀድስና ክቡርን እንዲወርስ በመሆኑም የቀደመ ሰው አዳምም አምላኩን እያመሰገነና በገነትም በጸሎት እየተጋ ኖሯል፡፡
በመጽሐፍ ቅዱስና በሌሎች ቅዱሳት መጻሕፍት ተመዝግቦ እንደምናገኘው ጥንተ ጠላት ዲያብሎስ አምላኩን ለማመስገን ባለመፍቀዱ ተረግሞ ወደ ምድር ከተጣለ በኋላ የሰውን ዘር በተለያዩ መንገዶች በማሳት፣ ከቀናው መንገድና ከጽድቁ ጎዳና በማስወጣት ፈጣሪያቸውን እንዳያገለግሉ ያደርጋል፡፡ (ዘፍ.፩-፰፣ አክሲማሮስ ዘዓርብ)
ይህ በእርግጥ አስከፊና አሳዛኝ ቢሆንም ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ለቅዱሳን ሐዋርያት ‹‹በዓለም ሳላችሁ መከራ አለባችሁ፤ ነገር ግን አይዞአችሁ፤ እኔ ዓለምን አሸንፌዋለሁ›› በማለት እንደ ነገራቸው ምንም እንኳን ጠላታችን መከራ አጽንቶና ተስፋ አስቆርጦ ብኩንና ከንቱ ሊያደርገን ቢጥርም መከራውን አልፈን፣ ሥቃያችንን ተቋቁመንና ችግራችን ተወጥተን በመልካም አገልግሎት ወደ አምላካችን መንግሥት መግባት ይቻለናል፡፡ (ዮሐ.፲፮፥፴፫)
መልካም አገልግሎት ለእግዚአብሔር አምላክ በሰውነታችን በበጎነታችን፣ በቅንነታችን፣ በትሕትናችን፣ በዕውቀታችንና በጉልበታችን የምናቅርበው የጸሎት፣ የጾም፣ የምጽዋት፣ የትሩፋትና የፍቅር አገልግሎት ነው፡፡ አምላካችንን ከማመስገን በተጨማሪ ዘወትር እርሱን በመፍራት በዕለት ኑሮአችን ልናስበውና ልናገለግለው ይገባል፡፡ ፈሪሃ እግዚአብሔር ያለው ሰው በምንም ዓይነት ሁኔታ ውስት ቢሆን ክፋትና ኃጢአት ከመሥራት ርቆ ይኖራልና፡፡ በቅንነትና በትሕትና የተሞላ የማኅበራዊ ሕይወትም ይኖረዋልና፡፡ ለሌሎች ሰዎችም መልካም ከማድረግ አይቦዝንም፡፡ ከዚህም አልፎ ተርፎ ባካበተው የመንፈሳዊ እና ዓለማዊ ዕውቀት እንዲሁም ባለው ጉልበት አምላኩን ዘወትር ያገለግላል፤ ይህም ተግባሩ ለጌታው የታመነ ታማኝና ቸር አገልጋይ ያሰኘዋል፡፡
በመጽሐፍ ቅዱስ የሐዲስ ኪዳን ክፍል ወንጌል ላይ ቅዱስ ማቴዎስ የጻፈውን አንድ ታሪክ እናንሣ፤ ‹‹አንድ ወደ ሌላ አገር የሚሄድ ባለጸጋ ባሮቹን ጠርቶ ያለውን ገንዘብ እንደ ሰጣቸው እንዲሁ ይሆናልና፤ ለእያንዳንዱ እንደ ዓቅሙ ለአንዱ አምስት መክሊት፣ ለአንዱ ሁለት፣ ለአንዱም አንድ ሰጠና ወደ ሌላ አገር ወዲያው ሄደ። አምስት መክሊትም የተቀበለው ሄዶ ነገደበት ሌላም አምስት አተረፈ፤ እንዲሁም ሁለት የተቀበለው ሌላ ሁለት አተረፈ። አንድ የተቀበለው ግን ሄዶ ምድር ቈፈረና የጌታውን ገንዘብ ቀበረ።››
ከብዙ ዘመንም በኋላ የእነዚያ ባሮች ጌታ መጣና ተቆጣጠራቸው። አምስት መክሊት የተቀበለውም ቀረበና ሌላ አምስት መክሊት አስረክቦ “ጌታ ሆይ፥ አምስት መክሊት ሰጥተኸኝ ነበር፤ እነሆ፥ ሌላ አምስት መክሊት አተረፍሁበት” አለ። ጌታውም “መልካም፥ አንተ በጎ ታማኝም ባሪያ፤ በጥቂቱ ታምነሃል፥ በብዙ እሾምሃለሁ፤ ወደ ጌታህ ደስታ ግባ” አለው።
ሁለት መክሊትም የተቀበለው ደግሞ ቀርቦ “ጌታ ሆይ፥ ሁለት መክሊት ሰጥተኸኝ ነበር፤ እነሆ፥ ሌላ ሁለት መክሊት አተረፍሁበት” አለ። ጌታውም “መልካም፥ አንተ በጎ፥ ታማኝም ባሪያ፤ በጥቂቱ ታምነሃል፥ በብዙ እሾምሃለሁ፥ ወደ ጌታህ ደስታ ግባ” አለው።
አንድ መክሊትም የተቀበለው ደግሞ ቀርቦ “ጌታ ሆይ፥ ካልዘራህበት የምታጭድ፣ ካልበተንህበትም የምትሰበስብ ጨካኝ ሰው መሆንህን አውቃለሁ፤ ፈራሁም ሄጄም መክሊትህን በምድር ቀበርሁት፤ እነሆ፥ መክሊትህ አለህ” አለ። ጌታውም መልሶ እንዲህ አለው፦ “አንተ ክፉና ሃኬተኛ ባሪያ፥ ካልዘራሁበት እንዳጭድ ካልበተንሁበትም እንድሰበስብ ታውቃለህን? ስለዚህ ገንዘቤን ለለዋጮች አደራ ልትሰጠው በተገባህ ነበር፤ እኔም መጥቼ ያለኝን ከትርፉ ጋር እወስደው ነበር። ስለዚህ መክሊቱን ውሰዱበት፤ ዐሥር መክሊትም ላለው ስጡት፤ ላለው ሁሉ ይሰጠዋልና ይበዛለትማል፤ ከሌለው ግን ያው ያለው እንኳን ይወሰድበታል።
የማይጠቅመውንም ባሪያ በውጭ ወዳለው ጨለማ አውጡት፤ በዚያ ልቅሶና ጥርስ ማፋጨት ይሆናል።›› (ማቴ.፳፭፥፲፬-፴)
ባለ ጸጋ የተባለው ጌታችን ነው፡፡ መክሊት የተባለው ደግሞ ከአምላካችን የተጠን የተለያዩ የአገልግሎት ጸጋዎች ናቸው፡፡ በታማኝነት ያገለገሉት ሰዎች ምሳሌ በምድራዊ ሕይወታቸው በተሰጣቸው ጸጋ በትጋት አምላካቸውን አገልግለው በመልካም ዕረፍት ገነት የገቡት ቅዱሳን ሰዎች ናቸው፤ መክሊቱን የቀበረው ሰነፍ አገልጋይ ደግሞ በተሰጣቸው ጸጋ በታማኝነት ማገልገል ሲገባቸው ያላገለገሉ ሰዎች ምሳሌ ነው፡፡
ጌታቸው ሊቆጣጠራቸው የመምጣቱ ነገር ጌታችን በዕለተ ምጽአት ለፍርድ ሲመጣ ለሁሉም በሠራው ሥራ መጠን ዋጋ ለመስጠት እንደሚመጣ የሚያመለክት ነው፡፡ ያገለገሉትን ታማኝ አገልጋየችም ለእያንዳንዱ ‹‹ወደ ጌታህ ደስታ ግባ!›› ማለቱ ታማኝ አገልጋዮች መንግሥተ ሰማያትን እንደሚወርሱ የሚያረጋግጥ ነው፡፡ ሰነፉ አገልጋይ ወደ ጨለማና ጥርስ ማፋጨት ወዳለበት ቦታ መወርወሩም ኀጥአን ወደ ገሃነመ እሳት መጣላቸውን የሚያሳይ ነው፡፡
ሊቁ ቅዱስ ያሬድ ‹‹ጌታውን ያስደሰተው አገልጋይ ታማኝና ቸር አገልጋይ ነው›› በማለት የተናገረው ይህን የወንጌል እውነት የሚገልጽ ነው፡፡ ታማኝነትና ቸርነት ለአገልግሎታችን እጅጉን አስፈላጊዎች ናቸው፡፡ ታማኝ መሆን ያለ ጥርጥርና በፍጹም እውነት ለአምላካችን መገዛት፣ መታዘዝና መኖር እንዲሁም በሕጉ መኖር ነው፡፡ ይህም ለእርሱ ታምነን ያለ ሐሰት፣ ያለ ስርቆት፣ ያለ አመንዝራነት እና ያለ ክህደት ወዘተ. እንድንኖር ይረዳናል፡፡ በተሰጠንም ክሂሎት፣ ተሰጥኦና ትሩፋት ማገልገል ያስችለናል፡፡ በአንደበታችን እንድናመሰግናው፣ በእጆቻችን አጨብጭበን፣ በጣቶቻችን በገና ደርድረንና መሰንቆ መትተን እንድንዘምርለት፣ በጉልበታችን እንድንሰግድለት በልባችን እንድናፈቅረው አስተምሮናል፡፡
ቸር በመሆን ለሌሎች በለጋስነት ካለን ነገር በመስጠትና በማካፈል መኖርን አሳይቶናል፡፡ አንድ ዳቦ ያለው ግማሹን ለሌላው እንዲያካፈል፣ ሁለት ልብስ ወይም ጫማ ያለው ለሌለው እንዲሰጥ፣ ከማዕዳችን ለተራቡ እንድናበላ፣ ከማድጋችን ለተጠሙ እንድናጠጣ፣ ለተቸገሩትና ላዘኑት ቸርነት በማድረግ እንድናስተዛዝን፣ የታመሙትን እንድናስታምም የአምላካችን ቅዱስ ቃል ያዘናል፡፡ እኛም እንደ መልካም ልጆቹ ለእርሱ በመታዘዝ ታማኝና ቸር አገልጋይ እንሁን!
የአምላካችን እግዚአብሔር ቸርነትና ረድኤት አይለየን፤ አሜን!
‹‹እኔ ባሪያህ የአባቴን በጎች ስጠብቅ አንበሳ ወይም ድብ ይመጣ ነበር፤ ከመንጋውም ጠቦት ይወሰድ ነበር፤በኋላውም እከተለውና እመታው ነበር፤ ከአፉም አስጥለው ነበር፤ በተነሳብኝም ጊዜ ጉሮሮውን አንቄ እመታውና እገድለው ነበር፡፡ይህም ፍልስጥኤማዊ ከነዚያ እንደ አንዱ ይሆናል፤ እንግዲህ እገድለው ዘንድ ከእስራኤል ተግዳሮትን አስወግድ ዘንድ ዛሬ አልሄድምን? የሕያው አምላክ ጭፍሮችን ይገዳደር ዘንድ ይህ ቆላፍ ምንድን ነው? ከአንበሳና ከድብ ያስጣለኝ እግዚአብሔር ከዚህ ያልተገረዘ ፍልስጥኤማዊ እጅ ያስጥለኛል››አለ፡፡ (፩ ሳሙ. ፲፯፥፴፬)
ዛሬስ ቢሆን በእስራኤል ዘነፍስ በምእመናን ላይ የሚገዳደሩ ብዙ ፍልስኤማውያን ተሰልፈዋል፤ እነዚህን ድል የሚነሣ በጎቹን ምእመናን ከተኩላ ከአንበሳና፣ ከድብ አፍ የሚታደግ ታማኝ አገልጋይ ማነው? ‹‹ከምእመናን ተግዳሮት የሚያርቅ ፈጣሪዬ ከመከራ ያድነኛል›› ብሎ የሚታመን የኢ-አማንያን ብዛት የማያስፈራው ማን ነው? ከትንሽነቱ እስከ ታላቅነቱ የታመነ አገልጋይ ማነው? ለተሾመበት ሓላፊነት ታማኝ ማነው? አሁንም ዓለማችን ከሥጋውያን ባለ ሥልጣናትም ሆነ ከመንፈሳዊያን መሪዎች የምትሻው ታማኝ ሰው ነው፡፡ በሙስና ያልተዘፈቀ ጉቦ አይኑን ያላጨለመበት ለመንጋው አርአያና ምሳሌ የሚሆን ሰው ታማኝ አገልጋይ ነው፡፡ በመኀላ የተቀበለውን የአገልግሎት ሓላፊነት የማይዘነጋ ታማኝ መሆን አለበት፡፡
መንጋው በክህደት ሲጠፋ ዝም ብሎ የሚያይ ጳጳስ፣ ቄስ፣ ዲያቆን፣ መምህር፣ ሰባኪ፣ አገልጋይ አይደለም፤ ታማሚው እየተሰቃየ የሚዝናና፣ ቆይ ሻይ ልጠጣ የሚል፣ ሐኪም ታማኝ አይደለም፡፡ ፍርድ የሚያጎድል ድሆችን የሚበድል ለደሃ አደጎች የማይፈርድ ዳኛ ታማኝ አገልጋይ አይደለም፡፡
ቅቤ በሙዝ እና በድንች ቀላቅሎ፣ በርበሬ በገል ጨምሮ ሌሎችን አጭበርብሮ የሚሸጥ ነጋዴ ታማኝ አገልጋይ አይደለም፡፡ እየነገደ ያለው በሰው ሕይወት መሆኑን መዘንጋት የለበትም፡፡ እንደየ አቅሙ በተሰጠው የአገልግሎት ዘርፍ ታማኝ መሆን አለበት፡፡
፫. ታማኝ አገልጋይ ቅዱስ ዮሴፍ
ዮሴፍ ለወንድሞቹ ምግባቸውን ተሸክሞ፣ የእርሱ ስንቅ ቢያልቅ የወንድሞቹን ስንቅ ሳይበላ በትንሽ የታመነ ሰው ነበር፤ ወንድሞቹ ሸጠውት በቤተ ጴጥፋራ በሚያገለግልበት ጊዜም ታማኝ ነበር፤ ታማኝነቱ በጲጥፋራ ቤት ጌታ አድርጎታል፡፡
‹‹ዮሴፍ ተሸጠ፤ አገልጋይም ሆነ፤ እግሮቹ በእግር ብረት ስለሰሉ ሰውነቱም ከብረት አመለጠች፤ ቃሉ ሳይደርስ የእግዚአብሔር ቃል ፈተነው፤ ንጉሥ ላከ፤ ፈታውም፤ የሕዝብ አለቃ አድርጎ ሾመው፤ የቤቱም ጌታ አደረገው፤ በገንዘቡ ሁሉ ላይ ገዢ አደረገው፡፡ አለቆቹን እንደ እርሱ ይገስጽ ዘንድ፣ ሽማግሌዎችን እንደ እርሱ ጥበበኞች ያደርጋቸው ዘንድ››፡፡ (መዝ.፻፬፥፲፯) በዚህ ሁኔታ የነበረው ዮሴፍ የጌታው ሚስት ሲወጣና ሲገባ ዐይኗን ጣለችበት በዝሙት አዐይን ተመለከተችው፡፡
‹‹የጌታውም ሚስት በዮሴፍ ላይ ዐይኗን ጣለችበት፤ ከእኔም ጋር ተኛ አለችው፤ እርሱም እምቢ አለ፡፡ ለጌታው ሚስቱ እንዲህ አላት፤ እነሆ ጌታዬ በቤቱ ያለውን ሁሉ ለእኔ በእጄ አስረክቦኛል፡፡ በቤቱ ያለውን ምንም የሚያውቀው የለም፤ በዚህ ቤት ከአኔ የሚበልጥ ሰው የለም፡፡ ሚስት ስለሆንሽ ከአንቺ በቀር ያልሰጠኝ ነገር የለም፤ እንዴት ይህን ትልቅ ክፉ ነገር አደርጋለሁ? እንዴትስ በእግዚአብሔር ፊት ኀጢአትን እሠራለሁ?››፡፡ (ዘፍ.፴፱፥፯)
በዮሴፍ ታማኝነት የጌታው ቤት ተባርኳል፤ ሀብቱ በዝቷል፡፡ በታማኝነቱ በቤቱ ያለውን ሁሉ ተረክቦ ነበር፤ የቀረበለት ፈተና ግን ከባድ ነበር፤ ይህን በታማኝነቱ ማለፍ ችሏል፡፡ ዛሬ በእያንዳንዱ ጓዳ ልጅ ብዙ ክፋት እንዲሁም በደል ይፈጸማል፡፡ ልጅ በፈላ ውኃ የሚቀቅሉም ሰዎች አሉ፤ ሥርቆትም የሚፈጽሙ በርካታ ናቸው፡፡ በጥቃቅን ዕቃዎች እንኳን የሚታመን ጠፍቷል፡፡ ዮሴፍ ግን በታማኝ አገልጋይነቱ በመጣበት መከራ ቢታሰር እንኳ ያለ ሹመት አላደረም፤ የእስረኞች አለቃ ነበር፡፡ ከእስር ቤት ሲወጣም ግብፅን በሙሉ መርቷታል፡፡ በግብፃውያን በሙሉ ተሾሟል፤ በጥቂቱ ታምኗልና፡፡ ‹‹በጥቂቱ የታመነ በብዙ ይሾማል›› እንዲል፡፡ (ማቴ.፳፭፥፳፬)
ከሦስቱ ታማኝ አገልጋዮች ሕይወት ሁሉም የሰው ልጅ ታማኝ አገልጋይነት የሚያሰጠውን ክብርና ጸጋ ተመልክቶ በታማኝነት ማገልገል ይገባዋል፡፡ ታማኝ መሆን መጀመሪያ የሚጠቅመው ለራስ ነው፤ ከዚያም ለሀገር፣ ለወገን፣ ለቤተ ክርስቲያን፣ ላመኑት፣ ላላመኑት ሁሉ ይጠቅማል፡፡ በመጨረሻም የጽድቅ አክሊልን ያቀዳጃል፤ መንግሥተ ሰማያትን ያወርሳል፤ በሰውም በእግዚአብሔርም ፊት ያስከብራል፡፡
ጻድቃን፣ ሰማዕታትና ቅዱሳን በታማኝ አገልግሎታቸው ፈጣሪያቸውን ደስ አሰኝተው ከብረዋል፡፡ በሓላፊው ገንዘብ ያልታመኑት ይሁዳ፣ ሐናንያ፣ ሰጲራ፣ የደረሰባቸውን ጉዳት አይተናል፤ በአካንረ ወልደ ከርሚንም ተመሳሳይ ቅጣት ደርሶበታል፡፡ (ሐዋ.፭፥፩፣ ፩፥፳፭)
ለዚህ ነበር ቅዱስ ዳዊት ‹‹አቤቱ፥ አድነኝ፥ ደግ ሰው አልቆአልና፥ ከሰው ልጆችም መተማመን ጎድሎአልና››ያለው፡፡ (መዝ.፲፩፥፩) ስለዚህ ሁሉም በአለበት የአገልግሎት መስክ ታማኝ አገልጋይ ሆኖ ‹‹አንተ በጎ ታማኝ አገልጋይ በጥቂቱ ታምነሃል፤ በብዙ እሾምሀለሁ›› የሚለውን የጌታውን የምስጋና ቃል መስማት ይገባዋል፡፡ መልካም አገልግሎት አገልግለን መንግሥቱን እንድንወርስና ‹‹ገብር ኄር›› እንድንባል አምላካችን ይርዳን፤ አሜን፡፡
ሐመረ ተዋሕዶ ሚዲያ ( አዳማ- ኢትዮጵያ)
ሚያዝያ 5 /2016ዓ.ም
ሼር በማድረግ አገልግሎታችንን ያሳልጡ ፔጁን ላይክ ያላደረጋችሁ ላይክ አድርጉ፡!
የTelegram:- ቻናሉን ይቀላቀሉ /channel/hameretewahedo
የYoutube:- ሰብስክራይቭ ያድርጉ https://www.youtube.com/channel/UCosQ9gywx0VAqiUm80oJ3rA
"ጾምን አጋመስነው አትበሉ"
ገብረ እግዚአብሔር ኪደ
ብዙ ሰዎች ደስ ተሰኝተውና እርስ በእርሳቸው፡- ግማሹን ጾም ፈጽመናል፤ የጾሙ እኩሌታ አለፈ ሲባባሉ ተመልክቻለሁ፡፡
💠እኔ ግን እነዚህ ሰዎች በዚሁ ምክንያት ደስ ሊላቸው እንደማይገባ እመክራቸዋለሁ፤
👉የጾሙ እኩሌታ ማለፉን ሳይኾን የኃጢአታቸው እኩሌታ መኼዱን መወገዱን ያስቡ፤ እንደዚያ ከኾነም ሐሴት ያድርጉ፡፡
👉ደስ ልንሰኝበት የተገባው ነገር ይኼ ነውና፡፡ ሊታይ የሚገባው ይኼ ነው፤ ጥንቱም እነዚህን ኹሉ ነገሮች የምናከናውናቸው ስሕተቶቻችንን እንድናስተካክል፣
👉ጾሙ ሲጀምር እንደ ነበርንበት ሳይኾን እንድንነጻበት፣
👉 ክፉ ልማዶቻችንን ወደ ጎን አድርገን የተቀደሰውን ምግባር ገንዘብ እንድናደርግ ነው
👉እንደዚህ ካልኾነ ግን ጾሙን መጨረሳችን በራሱ ለእኛ ታላቅ ጉዳትን ይዞ ከመምጣት ውጪ ሌላ ምንም ረብ ጥቅም አይሰጠንም፡፡
👉ስለዚህ ብዙ ጊዜ መጾማችንን ብቻ አንመልከት፤ ይህ ምንም ትልቅ ነገር አይደለምና፤ ይልቁንስ በዚህ ጾም ራሳችንን አሻሽለን እንደ ኾነ፣ ጾሙ ከተፈታ በኋላም የዚሁ ፍሬ ጎምርቶ ይታይብን እንደ ኾነ ሐሴት እናድርግ፡፡
👉የክረምት ጥቅሙ ይበልጥ የሚታወቀው ወራቱ ካለፈ በኋላ ነውና፡፡
👉የዚያን ጊዜ የአበባው ማበብ፣ የአዝመራው ማፍራት፣ ሌሎች ዕፅዋትም በቅጠላቸውና በፍሬያቸው በወርሐ ክረምት ያገኙትን ጥቅም ግልጽ አድርገው ይናገራሉና! በእኛም ዘንድ ልክ እንደዚህ ይኹን፡፡
👉በወርሐ ክረምቱ በብዛትም በዓይነትም የተለያየ ዓይነት የዝናብ ጠብታዎችን ተቀብለናል፤ ብዙ ተከታታይ ትምህርቶችን ተምረናል፤ መንፈሳዊ አዝርእት ተዘርተዉብናል፤ የቅምጥልነት እሾኽም ቈርጠን ጥለናል፡፡
👉ስለዚህ ጾሙ በተፈታ ጊዜ የጾሙ ፍሬ ይከብበን ዘንድ፣ ከጾሙ የሰበሰብናቸውን መልካም ነገሮችም ጾሙን ራሱን እናስታውሰው ዘንድ የሰማነውን ነገር አጽንተን በመያዝ እንትጋ።
"የተባረከ ሰው ማለት የራሱን ድክመት የሚያው ሰው ነው። ምክንያቱም ይሄ የእውቀቱ መሠረትና የሁሉም መልካም ነገሮች መጀመሪያ ይሆንለታልና፡፡"
(ማር ይስሐቅ)
ዛሬ
ወዳጄ ሆይ !በእግዚአብሔር የፍርድ ወንበር ፊት በግልጽ እንዳይወቅስህ ዛሬ ስለ ሠራሄው ኃጢአት ወደ ንስሐ የሚመራ ወቀሳን ይወቅስህ ዘንድ ቤትህን ዘግተህ ሕሊናህን ተቀስቅሰው !
ቅ ዮ አፈ ወርቅ
/channel/dnhayilemikael
❖ ተወዳጆች ሆይ የምታደምጡ ብቻ አትኹኑ፤ ያስተማርኳችሁን ትምህርት ለሌሎችም በማስተላለፍ መምህራን ትኾኑ ዘንድ ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ ✍️“አንዱ ሌላውን ያንጸው”
📖1ኛ ተሰ 5፥11
✍️ ዳግመኛም “በፍርሐትና በመንቀጥቀጥም የራሳችኁን መዳን ፈጽሙ” ብሎ እንደ ተናገረው በስሕተት ጐዳና ያሉትን ታድኑ ዘንድ መረባችሁን ጣሉ ብዬ እማፀናችኋለሁ።
📖ፊልጵ 2፥12
❖ ይህን ስታደርጉ ቤተክርስቲያን ከመቼውም ጊዜ በላይ ትሰፋለች፤ እኛም ይህን ዐይተን እጅግ ደስ እንሰኝባችኋለን፤ እናንተም ለወንድሞቻችሁ፣ ለእኅቶቻችሁ ባሳያችሁት ፍቅር በሰማያት ዘንድ ታላቅ ማዕረግና ክብር ታገኛላችሁ።
❖ እንደምታውቁት የእግዚአብሔር ፈቃድ እያንዳንዱ ክርስቲያን ስለ ራሱ መዳን ብቻ እንዲያስብ አይደለም፤ ወንድሙንም እንዲያንጽ ነው እንጂ፤ ሲያንጸውም በቃል ብቻ አይደለም፤ በተግባርም ጭምር እንጂ፤ የእግዚአብሔር ፈቃዱ እያንዳንዳችን በአኗኗራችን ክርስቶስን መስለን ታምነን እንድንኖርና ፍጥረት ኹሉ ወደ እግዚአብሔር መንግሥት እንዲገቡ ማድረግ ነው፡፡
❖ ይኸውም ሰዎች ከምንናገረው በላይ የምንኖረውን ስለሚያምኑና ስለሚማርካቸው ነው፤ ብዙውን ጊዜ በተዋቡ ቃላት ስለ ይቅርታ ብንናገር ነገር ግን በሕይወታችን እጅግ ቂመኞችና ይቅርታን የሚቀበል ልብ የሌለን ከኾነ ቃላችንና ሕይወታችን ስላልተስማማላቸው ሰዎች የምንለውን ነገር አያምኑንም፡፡
❖ የምንናገረውንና የምናስተምረውን የምንኖረው ከኾነ ግን ያምኑናል፤ እውነቱን ለመቀበልም አይቸገሩም፤ በቃል መነገሩ፣ በልብ መታሰቡ፣ በቅዱሳት መጻሕፍት መዘገቡ ከፍ ከፍ ይበልና ጌታችንና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስም እንዲህ ያለውን ክርስቲያን እንዲህ ሲል አመስግኖታል።
✍️“የሚያደርግም የሚያስተምርም እርሱ ንዑድ ክቡር ነው”
📖ማቴ 5፥19
❖ እንግዲህ ጌታችን ሲያስተምር በተግባር የሚሰጠውን ትምህርት በቃል ከሚሰጠው ትምህርት ይልቅ እንዳስቀደመው ታስተውላላችሁን? አያችሁ! ከተግባራችን በኋላ ቃላችን ባይከተል እንኳን ሰዎችን ወደ እውነት (ኢየሱስ) ለማምጣት በቂ ነው፡፡
❖ የቅድስና ሕይወት ለፈለገውና ለመረጠው ሁሉ ይቻላል፤ አሁን ካለንበት ደረጃ ከፍ ብለን የእግዚአብሔር ጸጋ በየልባችን እንዲሠራ እግዚአብሔር ፈቃዱ ነው፤ የእግዚአብሔር መንፈስ ነፍስን ወደ እግዚአብሔር በመምራት ልዩ ሀብቶችን በመስጠትና በረድኤት ከክርስቲያኖች ጋር ይሠራል።
❖ ቅዱሳን የሠሩት የእግዚአብሔር መንፈስ በውስጣቸው የሠራውን ነው፤ ታሪካቸውን ስታስብ በሕይወታቸው ውስጥ እግዚአብሔር እንዴት እንደሠራና በእነርሱ እንደተመሠገነ አስተውለሃል? የእነዚህ ሁሉ የጀግንነት ሥራዎቻቸው ምክንያትስ ገብቶሃል? በሚሠሩት ሥራ ሁሉ ከመንፈስ ቅዱስ ጋር ጠንካራ ሕብረት እንደነበራቸው አትረዳም?
📖2ቆሮ 13፥14
📌 ምንጭ
✍️ አቡነ ሺኖዳ ሣልሳዊ
/channel/dnhayilemikael
የእውነተኛ ክርስቲያን መገለጫው ምንድንነው ?
💠ፀሀይ ብርሃን ካልሰጠች ፀሀይ አትባልም ብርሃን አለመስጠት ተፈጥሯዋ አይደለምና
💠እንስሳት ካልተነፈሱ እንስሳት አይባልም መተንፈስ ተፈጥሯቸው ነውና 💠ዓሳ ከውኃ ከወጣ ሕይወት ያለው ሕይወት ያለ ዓሳ መሆኑ ይቅርና ይሞታል
✝️ አንድ ክርስቲያንም እውነተኛ ክርስቲያን የሚባለው :-
1/ ሲጸልይ ነው። ክርስቲያን ማለት በወልድ ውሉድ በክርስቶስ ክርስቶስ ክርስቲያን በመንፈስ ቅዱስ መንፈሳዊ ነውና ። ልጅ ከሆኑ ደግሞ አባት ማናገር ተፈጥሮው ነውና ።
2/ ሲያመሰግን ነው። ክርስቲያን ማለት እግዚአብሔር ፈጣሬ ዓለማት ብሎ የሚያምን ነው ። ስለዚህ ለአንድ ክረስቲያን የሰማይና የምድር ፍሬ እየተመለከተ እግዚአብሔርን ማመስገኑ ክርስቲያናዊ ተፈጥሮው ነው ።
3/ ሲመጸውት ነው ። ክርስቲያን ማለት ሀብት ሁሉ ከእግዚአብሔር እንደ ሆነ መመስከር ነው ። ስለዚህ ራስን እንደ መልእክተኛ አድርጎ በመቁጠር ያለውን ለሌለው ማካፈል ክርስቲያናዊ ተፈጥሮው ነው።
4/ ቅዱሳት መጻሕፍትን ማንበብ ነው ። ክርስቲያን በመንፈስ ቅዱስ ሀብት ደስ የሚሰኝ ነውና ። ይህን ለማድረግ መንፈስ ቅዱስ በቅዱሳት መጻሕፍት በኩል መናገር መስማት ለአንድ ክርስቲያን ክርስቲያናዊ ተፈጥሮው ነው።
ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ
(አምስቱ የንስሐ መንገዶችና ሌሎች =ከሚል መጽሐፍ የተወሰደ )
/channel/dnhayilemikael
የሰው ልጅ ሆይ፦
ሰው ቢጥልህ እግዚአብሔር ያነሳሃል፣ ሰው ቢጠላህ የፍቅር አምላክ ይወድሃል፣ ሰው ቢንቅህ የፈጠረህ አምላክ ያከብርሃል፣ ሰው ቢገፈትርህ ቸሩ አምላክህ ይደግፍሃል፣ ሰው ቢያስከፋህ አምላክ እርሱ ያጽናናሃል፣ ሰው ቢፈርድብህ እውነተኛው ዳኛ እግዚአብሔር ይፈርድልሃል።
ከሰው ያጣኸውን ከቸሩ አባትህ ከዓለም ፈጣሪ ከጌቶች ጌታ ከኃያሎች ኃያል ከነገሥታት ንጉሥ ከእግዚአብሔር ታገኛለህና ለዘለዓለም በእርሱ ታመን፡፡ እግዚአብሔር መልካም በመከራ ቀንም መሸሸጊያችን ነውና።
/channel/Meseretemedia
እንኳን ለመስቀለ ክርስቶስ ዓመታዊ ክብረ በዓል በሰላም አደረሳችሁ
በዚህች ቀን
ክብር ይግባውና የጌታችን የመድሐኒታችን የኢየሱስ ክርስቶስ መስቀል ለዘመናት ተቀብሮ
ከኖረበት የቆሻሻ ክምር ቦታ የወጣበት ቀን ነው።
በኦርቶዶክሳዊት ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን አስተምህሮ መሠረት የጌታችን
የአምላካችን የመድኃኒታችን የኢየሱስ ክርስቶስ የመስቀል በዓል ታላቅ ክብር
ይሰጠዋል፡፡ ይህም የመስቀል በዓልም ከዘጠኙ የጌታችን ንዑሳን በዓላት አንዱ ነው ።ለኛ
ለኦርቶዶክሳውያን መስቀል ማለት መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ዋጋ የከፈለበት ቤዛ
ዓለም የተከናወነበት እንደመሆኑ መስቀል በቤተ ክርስቲያናችን በሁሉ አገልግሎት ሰፊ
ድርሻ ያለውና እንዲሁም በንዋያተ ቅድሳት ላይ
የሚውል አቢይ ምልክት ነው:: በቤተክርስቲያን
አስተምህሮ “መስቀል” የሚለው ቃል ሦስት
መሠረታዊ ቁም ነገሮችን ያመለክታል።
የመጀመሪያው ጌታችን አምላካችን
መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የሰውን ልጅ
ከሞተ ነፍስ ለማዳን ሲል የተቀበለው መከራና
የከፈለው መሥዋዕትነት (የክርስቶስ መከራ
መስቀል) ነው፡፡ ሁለተኛው ደግሞ በክርስትና
ሕይወት ውስጥ የሚያጋጥም ልዩ ልዩ ዓይነት
መከራም (መከራ መስቀለ ክርስቲያን)
ነው፡፡ ሦስተኛው ደግሞ መድኃኒታችን
ኢየሱስ ክርስቶስ የተሰቀለበት ዕፀ መስቀል
ነው፡፡ መስቀል የሰላማችንና የድኅነታችን
የመቀደሳችን ዓርማ፣ ኢየሱስ ክርስቶስ የሰውን
ልጆች ለማዳን፥ የዘላለም ሕይወትን ለመስጠት
መስዋዕትነት የከፈለበት ቅዱስ ሥጋውን ክቡር
ደሙን ያፈሰሰበት መንበር፥ ሲሆን አምላካችንን
የምንመለከትበት መስታወት ነው። በዚህች ቀን
ክብር ይግባውና የጌታችን የመድሐኒታችን የኢየሱስ ክርስቶስ መስቀል ለዘመናት ተቀብሮ
ከኖረበት የቆሻሻ ክምር ቦታ የወጣበት ቀን ነው። ደገኛዋ እናት እሌኒ ቅድስት በመንፈስ
ቅዱስ አነሳሽነት :በቅዱስ ኪራኮስ መሪነት :በቅዱስ ሚካኤል ተራዳኢነት።
መስከረም 17
ቀን በደመራው ጢስ አማካኝነት የተጀመረው ቁፋሮ ከተጀመረ ከ 6 ወር ዕፀ መስቀሉ
ከቀበረ ከ 300 ዘመናት በኋላ መጋቢት 10 ቀን ተጠናቆ ቅዱስ መስቀሉ ወቶ
ብርሀን ለዓለሙ የበራበት ድንቅ ተአምራት የተደረገበት ቀን ነው ።ከ 10
አመት በኋላም ቤተ መቅደስ ተሰርቶ መስከረም 17 ቀን ቅዳሴ ቤቱ ከብሯል።
/channel/dnhayilemikael
#ትንሣኤ #ልቡና
ዛሬ የትንሣኤ በዓልን እያከበርን ነው። ትንሣኤ ማለት መነሣት ማለት ነው። ብዙዎቻችንም እንኳን ለብርሃነ ትንሣኤው አደረሰን እያልን ነው። ፖለቲከኛውም፣ ሰባኪውም፣ ጳጳሱም፣ ዘፋኙም፣ አርቲስቱም፣ አክቲቪስቱም ሁሉም እንኳን አደረሳችሁ እያለ ነው። ጌታ ተነሣ ስንል እኛም ትንሣኤ ልቡናን መነሣት አለብን። ፖለቲከኞች በቂም በቀል እና በሴራ መቃብር ውስጥ ሆናችሁ እንኳን አደረሳችሁ ብትሉን ራሳችሁን የምትዋሹ ትሆናላችሁ። ከመቃብር ውጡ። ትንሣኤያችሁን ሐዋርያት ይመልከቱት። በመቃብር ሆነን ስለ ትንሣኤ ብናወራ አያምርብንም።
።
ኑ በሉ ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ እንደተነሣ እኛም ትንሣኤ ልቡናን እንነሣ። የዘረኝነት፣ የውሸት፣ የጥላቻ፥ የበቀል፣ የሐሜት፣ የከንቱ ውዳሴ፣ የትዕቢት፣ የራስ ወዳድነት መቃብርን ፈንቅለን እንውጣ። ኑ እንነሣ። ስንነሣ ደግሞ ልባችን ብርሃንን ይሞላዋል። ችግሮቻችን ሁሉ ከእኛ በታች ነበሩ። ነገር ግን ትንሣኤ ልቡናን ባልተነሡ ሰዎች ምክንያት እንደ ተራራ የገዘፉ ሆኑብን።
ኑ በትንሣኤው እንነሣ።
በአፋችሁ እንኳን አደረሳችሁ እያላችሁን በልባችሁ ግን ቀጣይ ዓመት እንዳንደርስ እየገደላችሁን ከሆነ ይሁዳነት ነው። ይሁዳ በአፉ ሰላም እያለ ነው ጌታን የሸጠው። ሁሉም ከተንኮልና ከሽንገላ መቃብር ይውጣ እና የፍቅር ትንሣኤን ይነሣ።
© በትረ ማርያም አበባው
/channel/dnhayilemikael🌿
✝💚💛❤️✝💚💛❤️✝💚💛❤️✝💚💛❤️✝
በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ
አሜን
✍“ሕያውን ከሙታን መካከል ስለ ምን ትፈልጋላችሁ፤ ተነሥቶአል እንጂ በዚኽ የለም"
📖ሉቃ 24፥5
#ክርስቶስ_ተንስአ_እሙታን፤
በዐቢይ ኃይል ወስልጣን፤
#አሠሮ_ለሰይጣን፤
አግዐዞ ለአዳም፤
#ሰላም፤
እምይእዜሰ፤
#ኮነ፤
ፍሥሐ ወሰላም።
✥•••••●◉ ✞ ◉●•••••✥
ድርሳን ዘበዓለ ፋሲካ
✥•••••●◉ ✞ ◉●•••••✥
✍ "እግዚአብሔርን የሚያምንና የሚወድ ቢኖር፤ እርሱ በዚህ አንፀባራቂና የደስታ በዓል ደስ ይበለው"
✍ "ብልህ አገልጋይ ቢኖር፤ እርሱ ወደ ጌታው ሐሴት ገብቶ ዕልል ይበል፤ በጾም የደከመ ቢኖር፤ አሁን ደመወዙን ይቀበል፡"
✍ "በመጀመሪያው ሰዓት ወደ አምላኩ የቀረበ ቢኖር፤ ዛሬ ሽልማቱን ይውሰድ"
✍ "በሦስተኛው ሰዓት የመጣ ቢኖር፤ እርሱ በዓሉን በምስጋና ያክብር፤ በስድስተኛው ሰዓት የደረሰ ቢኖር፤ አይጎድልበትምና አይጠራጠር፤ እስከ ዘጠነኛ ሰዓት የዘገየ ቢኖር፤ ሳይጠራጠር ይቅረብ፤ እስከ ዐሥራ አንደኛዋ ሰዓት የዘገየ ቢኖር፤ ስለ መዘግየቱ አይደንግጥ፤ ጌታ ቸር ነውና፤ በመጨረሻ የመጣውንም እንደ መጀመሪያው አድርጐ ይቀበሏልና"
✍ "በዐሥራ አንደኛው ሰዓት ለመጣው ከመጀመሪያው ሰዓት አንሥቶ ሲደክም ከነበረው ጋራ እኩል ይሰጧልና፤ መጨረሻ ለመጣው ጌታ ምሕረቱን ይለግሰዋል፤ መጀመሪያ ለመጣውም ያስብለታል፡፡
✍ "ለአንደኛው ይሰጠዋል፤ ለሌላኛውም ጸጋውን ያድለዋል፤ ለአንደኛው መልካም ምግባሩን ይቀበልለታል፤ ለሌላኛውም መልካም ፍቃዱን ይቀበልለታል፤ ለአንዱ ምግባሩን ያከብርለታል፤ ለሌላኛውም በቅን ልቡና የሚያደርገውን ጥረት ያደንቅለታል"
✍ "ስለዚህ ኹላችሁም ወደ ጌታችሁ ደስታ ግቡ፤ ፊተኞች ኋለኞችም ሆይ እኩል ደመወዛችሁን ተቀበሉ፤ ባለጸጐች ድኾችም ሆይ በአንድነት ዘምሩ"
❖ እናንተ ብርቱዎች ደካሞችም ሆይ በዓሉን አክብሩት፡፡
✍እናንተ የጾማችሁ መጾም ያልቻላችሁም ሆይ ዛሬ ላይ ደስ ይበላችሁ፤ መሠዊያው ሙሉ ነውና ኹሉም በማዕዱ ደስ ይበለው፤ ፍሪዳው የሰባ ነውና አንድ ሰው ስንኳ እንደ ተራበ እንዳይሔድ፤ ኹላችንም የእምነት በዓሉን እንካፈል፤ ከቸርነቱና ከፍቅሩ ሀብትም እንቋደስ፡፡
✍ማንም ስለ ድኽነቱ አይዘን፤ ኵላዊቷ መንግሥት ተገልጣለችና፤ ማንም በኃጢአቱ አያንባ፤ ከመቃብሩ የይቅርታ ብርሃን ተንቦግቧልና፤ ማንም ሞትን አይፍራ የመድኃኒታችን ሞት ከዚህ ነጻ አውጥቶናልና፤ ለእርስዋ በመታዘዝም ጌታ አጥፍቷታልና፡፡
✍በሞቱ ሞትን ገደለው፤ ወደ ሲዖል በመውረድ ሲዖልን በዘበዘው፤ ኢሳይያስም አሰምቶ እንደ ተናገረ ሲዖል ከጌታችን ጋር ፊት ለፊት ተገናኘች፤
❖ መረራትም ከንቱ አድርጓታልና መረራት
❖ ሸንግሏታልና መረራት
❖ ሽሯታልና መረራት
❖ ነፍሳትን ይዛ እንዳታስቀር አስሯታልና መረራት
❖ መቃብር የዕሩቅ ብእሲ ሥጋ አገኘሁ ብላ ዋጠችው፤ስትውጠው ግን እግዚአብሔር ኾኖ አገኘችው መረራትም
❓ሞት ሆይ መውጊያህ ወዴት አለ
❓ሲዖል መቃብርም ሆይ ድል መንሣትህ ይዞም ማስቀረትህ ወዴት አለ
❖ ክርስቶስ ተነሣ፤
❖ ሞት ሆይ አንተም ጠፋህ
❖ ክርስቶስ ተነሣ፣ አጋንንትም አዘኑ
❖ ክርስቶስ ተነሣ፤ መላእክትም ሐሴት አደረጉ
❖ ክርስቶስ ተነሣ፤ የሰው ሕይወትም ነጻ ወጣች
❖ ክርስቶስ ተነሣ፤ መቃብርም ባዶ ኾነች
❖ ክርስቶስ ከሙታን ተለይቶ ተነሥቶ ለአንቀላፉት ኹሉ በኵር ኾኖላቿልና፡፡
❖ ለእርሱም ክብርና ጽንዕ ዛሬም ዘወትርም እስከ ዘለዓለሙ ድረስ ይኹን
✍ "ወምድርኒ ትገብር ፋሲካ
ተሐጺባ በደመ ክርስቶስ"
👉"ምድር ጸዳች ሐሴት አደረገች
በክርስቶስ ደም በእውነት ታጠበች"
እንኳን ለብርሃነ ትንሳኤው በሰላም በጤና አደረሳችሁ፤ አደረሰን መልካም በዓል
✍️"የሚሰማኝ ግን በእርጋታ ይቀመጣል ከመከራም ሥጋት ያርፋል"
📖ምሳ 1፥33
📌ምንጭ
✍ቅዱስ ዩሐንስ አፈወርቅ እንደፃፈው
✝💚💛❤️✝💚💛❤️✝💚💛❤️✝💚💛❤️✝
🙏 ለተጨነቀች ነፍስ ዕረፍት የሆነው የእግዚአብሔር ቃል ለሁሉ ይዳረስ ዘንድ፤ እኔም ለእናንተ ከአዘጋጀው በኃዋላ የተጣልሁ እንዳልሆን ስለ እኔ ጸልዩ
✍"ልብህን በእርጋታ አኑረው፤ የሁሉም መጨረሻ እና የሁሉም አገልጋይ ለመሆን በጣም ትጋ ለከንቱ ንግግር ዘገምተኛና ሰነፍ ሁን፤ ነገር ግን የቅዱሳት መጻህፍትን ቃል በማወቅ በመስማት ድኅነትን የሚሰጡ ናቸውና ብልህ ሁን"
📚ታላቁ ባስልዮስ ዘቂሳሪያ
ወስብሐት ለእግዚአብሔር
ይቆየን
───────────
Channel
🧲 /channel/dnhayilemikael🌿
FB /channel/dnhayilemikael🌿
የሰሙነ ሕማማት ዕለታት ስያሜዎች
፩ .ዕለተ ሰኑይ
መርገመ በለስ፡- ጌታችን የሆሣዕና ዕለት ቢታንያ አድሮ በማግስቱ ከቢታንያ ሲወጣ ተራበ፤ በመንገድም ሲያልፍ ቅጠል ያላት በለስን ከሩቁ ተመለከተ፡፡ ወደ በለሲቱም በቀረበ ጊዜ ከቅጠል በቀር አንዳች ፍሬ አላገኘባትም፡፡ ያንጊዜም ‹‹ከእንግዲህ ወዲህ ለዘለዓለም ከአንቺ ፍሬ የሚበላ አይኑር›› ሲል በለሲቱን ረገማት፡፡ ደቀ መዛሙርቱም ይህንን ሰሙት፡፡ በዚህም ምክንያት ይህች ዕለት በለሲቱ የተረገመችባት ቀን ናትና መርገመ በለስ ተብላ ትጠራለች፡፡ (ማር.፲፩፥፲፩-፲፬)
በዚህ አገላለጽ በለስ የተባለች ቤተ እስራኤል ስትሆን ፍሬ የተባለ ደግሞ ሃይማኖትና ምግባር ነው፡፡ መድኃኒታችን ክርስቶስ ከእስራኤል ፍቅርን፣ ሃይማኖትን፣ ምግባርን ፈልጎ አላገኘባቸውም፡፡ እስራኤል፦ ሕዝበ እግዚአብሔር፣ የአብርሃም ዘር መባልን እንጂ የአብርሃምን ሥራ በመሥራት በምግባር በሃይማኖት ጸንተው መኖር አይፈልጉምና ደግ ሰው አልተገኘባቸውም፡፡
በሌላ በኩል ደግሞ በለስ የተባለች ኦሪት ናት፡፡ ኦሪት በዚህ ዓለም ሰፍና ቢያገኛትም አማናዊ ድኅነትን የምታሰጥ ሆና አላገኛትም፡፡ ይሁን እንጂ በእርሷ ድኅነት ባይገኝባትም ‹‹ኦሪትና ነቢያትን ከመፈጸም በቀር ልሽር አልመጣሁም ልፈጽም እንጂ›› በማለት ሕገ ኦሪትን ፈጽሟታል፡፡ ከዚህም ባሻገር በለስ የተባለች ኃጢአት ናት፡፡ የበለስ ቅጠል ሰፊ እንደሆነች ሁሉ ኃጢአት በዚህ ዓለም ሰፍታ ሰፍና አግኝቷታል፡፡ በለስ ሲበሉት ይጣፍጣል፤ ቆይቶ ግን ይመራል፤ ኃጢአትም ሲሠሩት ለጊዜው ደስ ያሰኛል ኋላ ግን ያሳዝናል፡፡ በአንቺ ፍሬ አይገኝ የሚለውም በአንቺ በኃጢአት ፍዳ ተይዞ የሚቀር አይኑር ሲል ነው፡፡ በለሲቱ ስትረገም ፈጥና መድረቋም በአዳም ምክንያት ያገኘን በደል በእርሱ እንደጠፋልን ለመግለጽ ነው፡፡
/channel/dnhayilemikael🌿Читать полностью…
5 ነገሮችን በደንብ ያዙ።
1, 🛑አላማ
2 ,🛑እምነት
3,🛑ጥረት
4 🛑ጥንቃቄ
5🛑ጽናት
=>እነዚህን ያዟቸው ተጠቀሙባቸዉ ኑሯቸው።
❇️9ኙ የቅድስና መንገዶች❇️
፩👉ሃይማኖት
፪👉ጾም
፫👉ጸሎት
፬👉ስግደት
፭👉ምጽዋት
፮👉ፍቅር
፯👉ትህትና
፰👉ትዕግስት
፱👉የዋህነት
✝ንስሐ የተጣመመውን ያቀናል።በኃጥያት የቆሸሸውን ያነጻል፤ንስሐ ለሚገቡ ሁሉ የመላዕክት ንጹሕ ልብስ ይሰጣችኃል።
(ቅዱስ መቃርስ )
/channel/dnhayilemikael
ኃጢአት እንዳይሰለጥንብን ሁልጊዜ ወደ ሥጋ ወደሙ እንቅረብ
💠ቄርሎስ ዘኢየሩሳሌም የኩራትና የማንኛውም ዓይነት ክፉ ድርጊት
አንዳይሠለጥንብን ኹል ጊዜ ወደ ሥጋውና ደሙ ልንቀርብ ይገባናል ይለናል::
ሥጋውንና ደሙን ስንቀበል👉 ኃይል ሰማያዊን ገንዘብ እናደርጋል ይህ ደግሞ
ጠንካራ እንድንኾን ያደርገናል
ስንፍናችንን ያጠፋልናል በማለት ራስን
ለመቆጣጠር እንድንችል ምሰሶ የሚኾነን ቅዱስ ሥጋውንና ክቡር ደሙን
እንድንቀበል ወደ ድግሱ ይመራናል፡፡
💠በእርግጥ በሥጋውና ደሙ የክርስቶስ አካል እንኾናለን በእርሱም ኃይል የጠላትን ወጥመድ ሰባብረን እንጥላለን፡፡
መጽሔተ ወራዙት ዘኦርቶዶክስ ገጽ 226
/channel/dnhayilemikael
🌹🌹🌹🌹🌹#ዐይን_ይጹም🌹🌹🌹🌹🌹
ቤተክርስቲያናችን ሥርዓተ ጾምን ስትሠራ ከእህልና ውኃ እንዲሁም ከእንስሳት ተዋጽኦ ብቻ እንድንከለከል ሳይሆን የስሜት ሕዋሳቶቻችን ሁሉ ከልዩ ልዩ ገቢረ ኃጢአት መጾም እንዳለብን ታስተምረናለች፡፡ በአጠቃላይ የስሜት ሕዋሳቶቻችን ዐሥር ሲሆኑ አምስቱ ሕዋሳት በአፍኣ (የሚታዩ የሚዳሰሱ) ሲሆኑ ዐይነ ሥጋ፤ እዝነ ሥጋ፤ እግረ ሥጋ፤ እደ ሥጋና አንፈ ሥጋ ናቸው።
አምስቱ ደግሞ ውሳጣዊ ( የማይታዩ የማይጨበጡ ) ሲሆኑ እግረ ኅሊና፤ እደ ኅሊና፤ ዐይነ ኅሊና፤ አንፈ ኅሊናና እዝነ ኅሊና ናቸው አፋዊ ሕዋሳቶቻችን ከውሳጣዊው ሕዋሳቶቻችን ጋር ተናበዉ ከክፉ ነገር ሲርቁ ጾሙ እንላለን፡፡
ሥጋዊ ዐይናችን የሰውነታችን መብራት ሲሆን ኅሊናዊ ዐይናችን ደግሞ የኅሊናችንና የነፍሳችን መብራት ነው፡፡ በሥጋዊ ዐይናችን ዓለማዊ ነገሮችን ማየት ስንችል በኅሊናዊ ዐይናችን ደግሞ መንፈሳዊውን ረቂቁን ነገር መመልከት እንችላለንና፡፡ የሰውነታችን መብራት ዐይናችን እንደሆነ አምላካችን እግዚአብሔር በቅዱስ ወንጌል
"የሰውነት መብራት ዐይን ናት ዐይንህ ጤናማ ብትሆን ሰውነት ሁሉ ብሩህ ይሆናል ዐይንህ ግን ታማሚ ብትሆን ሰውነትህ ሁሉ የጨለመ ይሆናል፡፡ " ( ማቴ 6:22) በማለት አስተምሮናል፡፡
የሰው ልጅ የሕዋሳቱ ሁሉ መብራት በሆነችው ዐይኑ አይቶ መልካም ነገሮችን ከማድረግ ባሻገር ክፉ ነገሮችን ተመልክቶ ከእግዚአብሔር ጋር የሚያጣሉ ነገሮችን ከማድረግ እንዲከለከል ( እንዲጾም) ቅዱሳት መጻሕፍት ያስተምራሉ፡፡
አባታችን አዳም እና እናታችን ሔዋን ዕፀ በለስን በልተው ከገነት ለመባረራቸው ምክንያቱ ዐይናቸው ነበር በዐይናቸው ተመልክተው በመጎምጀታቸው ነው በተጨማሪም የሴት ልጆች መላእክትን መስለው ፈጣሪያቸውን እያመሰገኑ ከሚኖሩበት ከተቀደሰውና ከታላቁ ደብር ቅዱስ ወጥተው ከዘፋኞቹ ከቃኤል ልጆች ጋር በኃጢአት ለመውደቅ ያደረሳቸው ዐይናቸው ነው ምክንያቱም የኃጢአተኞቹን የቃኤልን ልጆች አስከፊ ዝሙት በዐይናቸው ከተመለከቱ በኋላ ነውና ወደ ገቢረ ኃጢአት የገቡት፡፡
በመሆኑም ዐይናችን ለሕዋሳቶቻችን ብርሃን ሆኖ የተሰጠን ሥነ ፍጥረትን እየተመለከትን ፈጣሪያችንን ልናደንቅበትና ልናመሰግንበት ጨለማውንና ብርሃኑን ገደሉንና ሜዳውን የምንመገበውንና የማንመገበውን የሚጠቅመንንና የማይጠቅመንን ልንለይበት የሚጠቅመንን እያየን ልንሠራበት እንጂ የምናየውን ክፉ ነገር ሁሉ እየሠራን ከፈጣሪያችን ጋር ልንጣላበት አይደለም፡፡
በዕለት ከዕለት ኑሮአችን በዐይናችን የምናየው ለኃጢአት ለርኩሰት ለሞት የሚጋብዝ ብዙ ጠቃሚ ያልሆኑ ነገሮች አሉ ለአብነት ያህል ብንመለከት እንኳን በማኅበራዊ ሚድያው የምናየው ነገር ዘግናኝና መንፈሳዊነታችንን የሚገዳደር ጉዳይ ነው ትውልዱም በማወቅም ይሁን ባለማወቅ በመገናኛ ብዙኃን ያየውን ነገር በመሥራት ራሱን እያረከሰና ከፈጣሪው ጋር እየተጣላ መሆኑን በየዕለቱ የምናየው ጉዳይ ነው፡፡
የዐይን ጾም ማለት ከእነዚህ ጠቃሚ ያልሆኑ ነገሮችን ከማየት መከልከል ማለት ነው፡፡ አምላካችን በቅዱስ ወንጌል " ዐይንህ ብታሰናክልህ ከአንተ አውጥተህ ጣላት" ያለበት ምክንያት የምታየውን ክፉ ሥራ ከመሥራት ተከልከል ማለቱ ነው፡፡ ምክንያቱም በምድር ላይ ዐይን ኖሮን ከገነት መንግሥተ ሰማያት ከምንባረር በምድር ላይ ዐይን ሳይኖረን ገነት መንግሥተ ሰማያትን ብንወርስ ይሻላልና፡፡ ጫማ ሰፊው ስምዖን ጫማ በሚሰፋበት ወስፌ ዐይኑን አውጥቶ የጣለበት ምክንያትም ይኸው መሆኑን መገንዘብ ያስፈልጋል፡፡
ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ለሐዋርያቱ ባስተማረው መጽሐፈ ኪዳን " አዑሩ አዕይንቲክሙ ዐይናችሁን ከልክሉ" አለ፡፡ አምላካችን ዐይናችሁን ከልክሉ ሲለን ግኡዝ ሆኖ ማራኪ መስሎ ኃጢአትን ይዞ የሚመጣ ነገርን እንዳያይ ሥጋዊ ዐይናችሁን ከልክሉት ክፉውን ነገር አይታችሁ እንዳላያችሁ ሁናችሁ ተውት የሚያስጎመጅ መስሎ የታያችሁን እንዳላያችሁ እለፉት ያያችሁትን ክፉ ነገር ሁሉ እናድርግ ፡ እንፈጽመው ከማለት ተቆጠቡ ሲል ታላቁ አባት አረጋዊ መንፈሳዊም ዐይናችን ከክፉ ነገሮች መጾም እንዳለበት እንዲህ በማለት ይመክረናል " ክላእ ንጻሬከ እምኩሉ ሥን ኀላፊ እንዘ ትኔጽሮ ለእግዚአብሔር ወትኄልዮ በልብከ በልብህ እግዚአብሔርን እያሰብህ ኃላፊውንና ጠፊውን ነገር ከማየት ዐይንህን ከልክል በማለት ያስተምረናል፡፡ ኃላፊውንና ጠፊውን ነገር በዐይናችን ዐይተን ወደ ልባችን ባመላለስነው ቁጥር እግዚአብሔርን ማሰብ አይቻልምና ነው፡፡
ኢትዮጵያዊው ሊቅ ቅዱስ ያሬድም " ይጹም ዐይን እምርእየ ኀሡም ዐይን ክፉ ነገርን ከማየት ይጹም " በማለት የዐይናችን ጾም ክፉ ነገር ከማየት መሆን እንዳለበት ገልጾልናል፡፡ በመሆኑም ዐይናችን ጠቃሚ ያልሆኑ ፊልምችን ድራማዎችን ማኅበራዊ መገናኛ ብዙኃንን በአጠቃላይ ለኃጢአት የሚጋብዙ ነገሮችን ከማየት ይልቅ መንፈሳውያን መጻሕፍትን በመመልከት ነፍሳችንን የማይጎዱትን መገናኛ ብዙኃን በማየት የመዝሙር ምስሎችን በማዘውተር ወዘተ መጾም ያስፈልጋል፡፡
ይቆየን።
#ይኽ_ትምህርት_ለሁሉም_የተዳረሰ_ይሆን_ዘን_ሼር_ላይክ_ኮመንት_እናድርገዉ_ቻናሉንም_ለብዙዎች_ተደራሽ_እያደረግን_የሚሰጡ_ትምህርቶችን_በማዳረስ_ሐዋርያዊ_አገልግሎት_እንስጥ
/channel/dnhayilemikael
መኑ ውእቱ ገብር ኄር : በጎ ቸር አገልጋይ ማን ነው?››
-----------------------------
በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ስያሜ የዐቢይ ጾም ስድስተኛው እሑድ ወይም ሳምንት ገብር ኄር ይባላል፤ ስያሜውን የሰጠውም ኢትዮጵያዊ ሊቅ ቅዱስ ያሬድ ነው፡፡ ከአምስቱ መጻሕፍቶቹ አንዱ በሆነው ጾመ ድጓ የዐቢይ ጾም ሳምንታት ስያሜዎች ከነሥርዓተ ማኅሌቱ አዘጋጅቷል፡፡ ስለዚህ በስድስተኛው የዐቢይ ጾም ሳምንት ከዋዜማው ቅዳሜ ጀምሮ በቤተ ክርስቲያን የሚዘመረው ዝማሬ፣ የሚሰበከው ስብከት፣ የሚሰጠው ትምህርት ገብር ኄርን ወይም ታማኝ አገልጋይን የሚያወሳ ነው፡፡
ለዚህም ምሳሌ እንዲሆነን በማቴዎስ ወንጌል ላይ የተጻፈው ታሪክ እናነሳለን፤ አንድ ባለ ጸጋ ሰው ባሪያዎችን ጠርቶ ለአንዱ አምስት መክሊት ሰጠው፣ ሁለት መክሊት የሰጠውም አለ፣ አንድ መክሊትም የሰጠውም አለ፡፡ ከዚህ በኋላ ወደሩቅ አገር ሄደ፡፡ አምስት መክሊት የተቀበለውም ወጥቶ ወርዶ ሌላ አምስት አትርፎ ዐስር አደረገ፡፡ ሁለት የተቀበለውም አትርፎ አራት አደረገ፡፡ አንድ የተቀበለው ግን ሄዶ መሬቱን ቆፍሮ በሻሽ ጠቅልሎ የጌታውን መክሊት ቀበራት፡፡
ከብዙ ጊዜ በኋላ ጌታቸው መጥቶ ተቆጣጠራቸው፡፡ አምስት መክሊት የተቀበለው ቀርቦ ‹‹ጌታዬ አምስት መክሊት ሰጥተኸኝ ነበር፤ እነሆ አምስት አተረፍኩ አለው፡፡ ‹‹ገብር ኄር ወምእመን ዘበሁድ ምእምነ ኮንከ ዲበ ብዙህ እሰይመከ ባዕ ውስተ ፍስሐሁ ለእግዚእከ፤ አንተ ታማኝ ባሪያ በጥቂቱ ታምነሃል፤ በብዙ እሾምሃለሁ፤ ወደ ጌታህ ደስታ ግባ›› አለው፡፡ ሁለት የተቀበለውም ቀርቦ ‹‹ጌታዬ ሁለት መክሊት ሰጥተኸኝ ነበር፤ እነሆ ወጥቼ ወርጄ ሌላ ሁለት አትርፌ አራት አድርጌአለሁ፡፡ አንተ ታማኝ በጎ አገልጋይ በጥቂቱ ታምነሃል፤ በብዙ እሾምሃለሁ ወደ ጌታህ ደስታ ግባ›› አለው፡፡
አንድ መክሊት የተቀበለው ግን ቀርቦ ‹‹ጌታዬ አንተ ክፉና ጨካኝ ካልዘራህበት የምታጭድ ካልበተንህበት የምትሰበስብ እንደሆንክ ስለአወቅሁ መሬቱን ቆፍሬ ቀበርኋት እነኋት መክሊትህ አለው፡፡ አንተ ሰነፍ ባሪያ መክሊቴን በጊዜ ልትሰጠኝ በተገባህ ነበር፤ እኔም ወጥቶ ወርዶ ለሚያተርፍ በሰጠሁት ነበር፡፡
የዚህን መክሊት ውሰዱና አስር መክሊት ላለው ስጡት፡፡ላለው ይሰጡታል ይጨመርለታል፤ለሌለው ግን ያለውን ይቀሙታል፡፡ይህን ሰነፍ ባሪያ እጅ እግሩን አሥራችሁ ጽኑዕ ጨለማ ወደአለበት ውሰዱት፤ጩኸትና ጥርስ ማፋጨት ወዳለበትም ጨምሩት››አለ፡፡(ማቴ.፳፭፥፲፬-፳፭)
ባለ ጸጋ የተባለው ጌታ ነው፤ መክሊት የተባለው ልዩ ልዩ የአገልግሎት ጸጋ ነው፡፡ ያተረፉት በሚገባ በታማኝነት ያገለገሉ ቅዱሳን ሰዎች ናቸው፤ መክሊቱን የቀበረው ደግሞ በታማኝነት በተሰጠው ጸጋ ማገልገል ሲገባው ያላገለገለ ነው፡፡ ጌታቸው ሊቆጣጠራቸው መጣ ማለት በዕለተ ምጽአት ለሁሉም በአገለገለው አገልግሎት ዋጋ ለመስጠት እንደሚመጣ ያሳየናል፡፡
ያገለገሉትን ወደ ጌታህ ደስታ ግባ አላቸው ማለት ታማኝ አገልጋዮች መንግሥተ ሰማያትን ይወርሳሉና፡፡ ሰነፎች ደግሞ ጥርስ ማፋጨት ስቃይ ጽኑዕ ጨለማ ባለበት ሲዖል መግባታቸውን የሚያሳይ ነው፡፡
ከላይ ያነሳነው የቅዱስ ወንጌል ቃል ‹‹ታማኝ አገልጋይ ማነው?›› ይህ እያንዳንዱ በአርዓያ እግዚአብሔር የተፈጠረ የሰው ልጅ ጥያቄ ነው፤ የዚህን አምላካዊ ጥያቄ መልስ መስጠት ከሰው ልጆች ይጠበቃል፡፡
ታማኝ አገልጋይ ማነው?
፩. ታማኝ አገልጋይ ነቢዩ ሙሴ
ሙሴ ታማኝ አገልጋይ እንደነበር ቅዱሳት መጻሕፍት ይመሠክራሉ፡፡ ‹‹በመካከላችሁ ነቢይ ቢኖር እኔ እግዚአብሔር በራእይ እገለጥለታለሁ ወይም በህልም አናግረዋለሁ፤ ባሪያዬ ሙሴ ግን እንዲህ አይደለም፤ እርሱ በቤቴ ሁሉ የታመነ ነው››፡፡ (ዘኁ.፲፪፥፮) ይህ የፍጡር ምስክርነት ሳይሆን በፈጣሪው የተሰጠ ምስክርነት ነው፡፡ በእውኑ በዘመናችን እንኳን ፈጣሪ ፍጡራን ታማኝነቱን የሚመሰክሩለት አጋልጋይ ይኖር ይሆን? የሙሴን ታማኝ አገልጋይነት በረሃ፣ ስደት፣ መከራ እና ቁጣ ያልበገረው አርባ ዓመት ስለ ወንድሞቹ በመሰደድ፣ አርባ ዓመት ደግሞ የተሰደደላቸው ወንድሞቹን በመምራት ባሕር በመክፈል፣ ጠላት በመግደል፣ መና በማውረድ፣ ደመና በመጋረድ ውኃ ከዓለት አፍልቆ በማጠጣት፣ መከራውን ከወገኖቹ ጋር በመቀበል፣ የቀኑ ሀሩር የሌሊቱን ቁር /ብርድ/ ታግሶ በታማኝነት አገልግሏል፤ ታማኝነቱ እስከሞት ነበር፡፡
‹‹ሙሴም ወደ እግዚብሔር ተመልሶ ወዮ እኒህ ሕዝብ ታላቅ ኀጢአት ሠርተዋል፡፡ ለራሳቸውም የወርቅ አማልክት አድርገዋል፡፡ አሁን ይህን ኀጢአታቸውን ይቅር በላቸው፤ ያለዚያ ግን ከጻፍከው መጽሐፍ እባክህ ደምስሰኝ፤ ከባለሟልነትህ አውጣኝ››፡፡(ዘጸ.፴፪፥፴፩) ታማኝ አገልጋይ ‹‹እኔ ልሙት፤ ሌሎች ይዳኑ የሚል ነው፤ አሁን የምናየው ግን ፈጽሞ ከዚህ የተለየ ነው፡፡ ሰዎች ይሙቱ፤ እኔ ልኑር፤ ሰዎች ጾም ይደሩ፤ እኔ ልብላ፤ ሰዎች ይራቆቱ እኔ ልልበስ፤ ሰዎች ይዘኑ፤ እኔ ልደሰት›› ነው፡፡
ታማኝ አገልጋይ ለሚያገለግላቸው ሰዎች ጥቅም ቅድሚያ የሚሰጥ እንጂ የራሱን ጥቅም የሚያስቀድም አይደለም፡፡ ዛሬ በዓለማችን የምንመለከተው ግን ‹‹ጩኸት ለአሞራ መብል ለጅግራ›› የሚባለውን መሰል ነው፡፡ በታማኝ አገልጋዮች ድካም የሚሸለሙ ታማኝ አገልጋዮች በሠሩት ሥራ የሚያቀርቡ፣ የሚወደሱ፣ ከጥቅሙ እንጂ ከድካሙ መክፈል የማይሹ እንቅፋት የሚመታው እግርን ነው፡፡ አክሊል የሚቀዳጀው ግን ራስ ነው፡፡ ታማኝ አገልጋይ ማለት እንደራስ አክሊል ዘውድ የሚጸፋ ብቻ ሳይሆን እንደ እግር እንቅፋቱን፣ እሾሁን፣ መከራውን፣ ውጣ ውረዱንና ድካሙን የሚቀበል ነው፡፡ በጥቅም ጊዜ ለራሱ በአካፋ የሚዝቅ ወይም በጭልፋ የሚጨለፍ አይደለም፡፡ ሙሴ ባሕር የከፈለው፣ መና ያወረደው፣ ደመና የጋረደው፣ ወይም ውኃ ያፈለቀው ለራሱ አልነበረም፤ ለሚመራቸው ሕዝብ ነበር እንጂ፡፡ ታማኝ አገልጋይ ያሰኘውም ይኸው ነው፤ በዚህ ከብሮበታል፤ ተመስግኖበታልም፡፡
፪. ታማኝ አገልጋይ ነቢዩ ዳዊት
ዳዊት ዘመነ መሳፍንት አልፎ ዘመነ ነገሥት ሲተካ እስራኤልን በንጉሥነት እንዲያገለግል እግዚአብሔር ከበግ ጥበቃው ወስዶ ሥልጣን ሰጠው፤ ያልተመነ የሳዖልን በትረ መንግሥት በሳሙኤል እጅ ተቀብቶ ተቀብሏል፡፡
በተሰጠው ሥልጣን በታማኝነት ሕዝበ እስራኤልን መርቷል፡፡ ታማኝነቱንም እግዚአብሔር ለሙሴ እንደ መሰከረለት ለእርሱም መስክሮለታል፡፡ ‹‹እግዚአብሔር እንደልቡ የሆነ ሰው መርጧልና››፤ ‹‹የዘይቱን ቀንድ ሞልተህ በልጆቹ መካከል ለእኔ ንጉሥ አዘጋጅቻለሁና ወደ እሴይ ወደ ቤተልሔም እልክሃለሁ›› እንደተባለው፡፡ (፩ ሳሙ.፲፫፥፲፫፣ ፲፮፥፪)
‹‹ወረከብክዎ ለዳዊት ገብርየ ወቀባዕክዎ ቅብዐ ቅዱስ›› እንዲል፡፡(መዝ.፹፰፥፳) ‹‹ባሪያዬ ዳዊትን አገኘሁት፤ የተቀደሰ ዘይትንም ቀባሁት›› ይህን አባ ጊዮርጊስ ዘጋስጫ ሰዓታት በተባለው ድርሰቱ፡- ‹‹ረከብክዎ ለዳዊት ገብርየ ብዕሴ ምእመነ ዘከመልብየ›› አገልጋዬ ዳዊትን እንደ ልቤ የታመነ ሰውን ሆኖ አገኘሁት›› ሲል ተርጉሞታል፡፡ የተገኘው በታማኝነት ነበር፤ ከነገሠ በኋላም ታማኝ ነበር፤ አሁን በዚህ ዓለም የምንኖር እኛ ግን በድኅነት ታማኝ እንሆንና ሀብት ሹመት ሥልጣን ሲመጣ ታማኝነትን እናጣለን፤ እንዲያውም ታማኝነትን እንንቀዋለን፡፡ መስረቅ ጀግንነት፣ መዋሸት ሥልጣኔ ይመስለናል፡፡ ዳዊት ሳይሾም በጎቹን በመጠበቅ ታማኝ ነበር፡፡ በጎቹን የሚነጥቅ ተኩላ አንበሳ ቢመጣ በኋላው ተከትሎ ነብሩን በጡጫ አንበሳውን በእርግጫ ብሎ በጎቹን ያስጥለው ነበር፡፡
ይህን ያህል ቀን ጾምኩ አትበሉኝ፡፡
💠 ይህን አልበላሁም ወይም ያንን አልበላሁም፣
💠የወይን ጠጅ አልጠጣሁም አትበሉኝ።
👉ይልቁንስ ከግልፍተኝነት ወደ ገርነት፣
👉 ከጭካኔ ወደ ደግነት የተሸጋገርኽ እንደሆነ አሳየኝ፡፡
👉በአንተ ውስጥ ጥላቻና ቂም ቢኖሩ፣
👉 በወይን ፋንታ ውኃ ብትጠጣ ምን ይጠቅማል?
👉ጾም ብቻውን ስማያዊ ምንዳ አያስገኝምና፤
👉 ትርጉም በሌለው በባዶ የፆም ሥርአት ራስህን አታስገዛ።
#ቅዱስ_ዮሐንስ_አፈወርቅ
+ ተራ የማይደርሰው ተጠማቂ +
"ከሠላሳ ስምንት ዓመት ጀምሮ የታመመ አንድ ሰው ነበረ፤ ኢየሱስ ይህን ሰው ተኝቶ ባየ ጊዜ፥ እስከ አሁን ብዙ ዘመን እንዲሁ እንደ ነበረ አውቆ፦ ልትድን ትወዳለህን? አለው ሰውዬውም፦ ጌታ ሆይ፥ ውኃው በተናወጠ ጊዜ በመጠመቂያይቱ ውስጥ የሚያኖረኝ ሰው የለኝም ነገር ግን እኔ ስመጣ ሳለሁ ሌላው ቀድሞኝ ይወርዳል፡ ብሎ መለሰለት" ዮሐ.5:5-7
ይህንን ጥያቄና መልስ ሳይ በሽተኛውን ማናገር ያምረኝና እንዲህ በል ይለኛል :-
አንተ በሽተኛ ግድ የለህም የተጠየቅከውን ብቻ መልስ:: እመነኝ ጠያቂህ ተራ ጠያቂ አይደለም:: የሚጠይቅህ ሲያደርቁህ እንደኖሩት ሌሎች አሰልቺ ጠያቂዎች አይደለም:: ጥያቄውም የሌሎችን ሰዎች ዓይነት ጥያቄ አይደለም:: ከፊትህ የቆመው የመጠመቂያውን ውኃ ብቻ ሳይሆን በዓለም የሞላውን ውኃ የፈጠረ አምላክ ነው::
"ወደ መጠመቂያው የሚያኖረኝ ሰው የለኝም" አልክን? የተጠየቅከውን መልስ እንጂ! ወደ መጠመቂያው መግባት ትወድዳለህን? ብሎ ማን ጠየቀህ? የጠየቀህ ማን እንደሆነ ባታውቅ እንኩዋን ጥያቄውን እንኳን በደንብ ስማ እንጂ!
ሰው የለኝም አትበለው : ስለመጠመቂያው ወረፋ አትንገረው : ስንት ሰው ቀድሞህ እንደዳነ አትቁጠርለት:: የጠየቀህ ግልፅ ጥያቄ ነው::
ልትድን ትወዳለህን?
እግዚአብሔር ፊት ስለ ችግርህ ክብደት ለምን ታወራለህ? ምን እንደሌለህማ እሱም ያውቃል:: አዎን እድን ዘንድ በለው:: ችግርህን ትተህ የምትፈልገውን ንገረው:: የችግርህ መወሳሰብና ሥር መስደድ ለእሱ የሚከብድ አይደለምና መዳን እንደምትሻ ብቻ በእምነት ንገረው የሚል ተግሣፅ በበሽተኛው በኩል ወደ እኛ ደረሰ::
🛌🛌🛌🛌🛌🛌🛌🛌🛌
መጻጉዕ (በሽተኛው) ቤተ ሳይዳ ከመጣ 38 ዓመት ሆነው:: ዳዊትና ሰሎሞን 40 40 ዓመት ነግሠው እንኳን ብዙ የምሬት ቅኔ ተቀኝተዋል:: ይህ ሰው አልጋ ላይ ሆኖ አርባ ዓመት ሊሞላው ሲል ምንኛ ተንገሽግሾ ይሆን?
ልብ በሉ ጌታችን በቤተልሔም ሲወለድ ይህ በሽተኛ በአልጋው ላይ ነበረ:: እረኞች ከብዙ መላእክት ጋር ሲዘምሩ እሱ የአንድን መልአክ መውረድና ውኃውን ማናወጥ እየጠበቀ ስድስተኛ ዓመቱን ደፍኖ ነበር:: ጌታችን የሠላሳ ሁለት ዓመት ዕድሜ ላይ ደርሶ ወደ መጠመቂያው ሥፍራ ሲመጣም ይህ ሰው አልጋው ላይ ነው:: መጠመቂያዋን 38 ዓመት በተስፋ ሲጠብቅ ቆይቶ ሳይጠመቅባት ቀረ::
ጌታ ሆይ የማይደርሰኝን ወረፋ ከመጠበቅ አድነኝ:: እንድፈወስበት ባልፈቀድክበት ሥፍራ ዕድሜዬን እንዳልጨርስ ጠብቀኝ::
ወደ ሐዲስ ኪዳንዋ ቤተ ሳይዳ ወደ ቤተክርስቲያን ከመጣሁ ብዙ ዘመን አስቆጠርኩኝ:: ግን እስካሁንም ድረስ ከኃጢአት አልጋ ላይ አልወረድሁም:: መነሣት እፈልጋለሁ ግን አቃተኝ:: ልቤ እንጂ እግሬ ጸንቶ መቆም አልቻለም::
ፈረቃ የሌለብህን የሕይወት ውኃ አንተን ሊጠጡ ሲመጡ በዓይኔ እየተቀበልኩ ብዙዎች ጠጥተውህ ሲድኑ በዓይኔ እየሸኘሁ አልጋዬ ላይ ቀረሁ::
እኔ እንደተኛሁ ስንቱ ቀድሞኝ እንደዳነ ባየህልኝ:: ከእኔ በኁዋላ መጥተውስ ከእኔ በፊት ስንቶች ዳኑ?
ስንቱ ከኃጢአት አልጋ በንስሓ ተነሥቶ ያንተን ሥጋና ደም ተቀብሎ ተፈወሰ?
የቤተ ሳይዳው ሐኪም ሆይ ወደ አንጋፋው በሽተኛህ ወደ ጽኑዕ ሕመምተኛህ ወደ እኔ የምትመጣው መቼ ይሆን? ያን ሕመምተኛ "ብዙ ዘመን እንዲሁ እንደነበረ" አውቀህ ያናገርከው ሆይ እኔን የምታናግረኝ መቼ ይሆን? እኔስ ብዙ ዘመን እንደሆነኝ አታውቅምን? ሰው የለኝም : ልብ የለኝም : ኃይል የለኝም : አቅም የለኝም ብዬ ብሶቴን የምነግርህ መቼ ይሆን?
"ኢየሱስ፦ ተነሣና አልጋህን ተሸክመህ ሂድ፡ አለው። ወዲያውም ሰውዬው ዳነ አልጋውንም ተሸክሞ ሄደ" ዮሐ.5:8-9
አንተ ተነሥ ብለኸው የማይነሣ ማን ነው? እንኳንስ ከአልጋ ከመቃብርም ተነሥ ያልከው ይነሣ የለምን?
ግዴለህም እኔንም ተነሥ በለኝ:: ተነሥ ኃይልን ልበስ ያልከኝ እንደሆነ እንኳንስ "ሸክሜም ቀሊል ነው" ያልከው አንተ ያዘዝከኝ የራሴን ሸክም ቀርቶ የወንድሜን ሸክምም ተሸክሜ የአንተን ሕግ እፈጽማለሁ:: (ገላ. 6:2)
🛌🛌🛌🛌🛌🛌🛌🛌
"ወዲያውም ሰውዬው ዳነ አልጋውንም ተሸክሞ ሄደ። ... ከዚህ በኋላ ኢየሱስ በመቅደስ አገኘውና፦ እነሆ፥ ድነሃል፤ ከዚህ የሚብስ እንዳይደርስብህ ወደ ፊት ኃጢአት አትሥራ፡ አለው" ይላል::
በሽተኛው ድኖ አልጋውን ተሸክሞ እንደሔደ ሳነብ አንድ ነገር ልቤን አስጨነቀው:: ይህ ሰውዬ 38 ዓመት ሙሉ የኖረው በቤተ ሳይዳ ነው:: ክርስቶስ ድንገት ፈውሶት ሒድ ሲለው እሺ ብሎ ከዚያ መጠመቂያ ሥፍራ ከወጣ በኁዋላ ወዴት ሔደ?
የሠላሳ ስምንት ዓመት ሕመምተኛው ሆይ እውነት ወዴት ሔድህ? ከመጠመቂያው መውጣትህን ሰምተን አድንቀናል:: ከዚያስ ወዴት ሔድክ? ዙሪያ ገባው አልተለወጠብህም? መንገድስ አልጠፋብህም?
ወደ ዘመዶች ቤት ሔድክ እንዳልል "ሰው የለኝም" ስትል ሰምቼሃለሁ::
አልጋህንስ የት አደረስካት? መቼም ሰባብረህ እንደማትጥላት የታወቀ ነው:: አልጋ ለታመመ ብቻ ሳይሆን ለጤነኛም ያስፈልጋልና አራት እግር እያላት ጥላህ ያልሔደችውን ዘመድህን መቼም በክብር ማስቀመጥህ አይቀርም::
ለማንኛውም እዚያው ምዕራፍ ላይ ኢየሱስ ይህንን በሽተኛ ዳግም በመቅደስ አገኘው ይላል:: ዮሐ. 5:14 ጌታ ከመጠመቂያ ቦታ አድኖ ያስነሣውን ሰው በመቅደስ ቆሞ አገኘው:: ይህ በሽተኛ እግሩ ሲጸናለት የሔደው ወደ ፈጣሪ ደጅ መሆኑ ያስመሰግነዋል::
ጌታ በመጠጥ ቤት ቢያገኘው ኖሮ ያሳዝን ነበር:: እግርህን ያጸናሁልህ ለዚህ ነው ወይ ብሎ ባዘነበት ነበር:: አሁን ግን ያዳነው ጌታ በመቅደስ አግኝቶት "እነሆ ድነሀል ከዚህ የሚብስ እንዳይደርስብህ ወደ ፊት ኃጢአት አትሥራ" አለው::
ይህንን የምታነብ ወንድሜ ሆይ ክርስቶስ አንተንስ አላዳነህም? "ኸረ እኔ ሽባ ሆኜ አላውቅም:: ማንም እኔን ከአልጋ አላስነሣኝም ትለኝ እንደሆን እመነኝ ክርስቶስ እንደ አንተ ያዳነውስ የለም:: እርሱ እኔና አንተን ተነሡ ብሎ ያስነሣን ከ38 ሳይሆን ከዘላለም የሲኦልና የኃጢአት አልጋ ነው::
እኛን የፈወሰን አልጋችንን አሸክሞ ሳይሆን እሱ ራሱ እኛን ከነአልጋችን ተሸክሞን ነው:: ካላመንከኝ ነቢዩ ኢሳይያስን ጠይቀው "እርሱ ግን የብዙ ሰዎችን ኃጢአት ተሸከመ" ሲልህ ትሰማዋለህ:: ኢሳ. 53:12 የእኛን በደል ተሸክሞ ጀርባው ምን ያህል እንደ ቆሰለ ባየህ:: ይህንስ ጀርባዬን ታያለህ የተባለውን ሙሴን ብትጠይቀው ሳይሻል አይቀርም::
ያዳነህ አምላክ አንተንስ የት ነው የሚያገኝህ? እንደዚህ ሰውዬ መቅደስ ያገኝህ ይሆን?
የትም ቢያገኝህ ግን ቃሉ አንድ ነው "እነሆ ድነሀል ከዚህ የሚብስ እንዳይደርስብህ ወደ ፊት ኃጢአት አትሥራ" ከሠላሳ ስምንት ዓመት የአልጋ ቁራኝነት የሚብስ ምን ሊመጣ ነው? ካልክስ እሱን ከማየት ይሠውረኝ ብትል ይሻልሃል::
ዲያቆን ሄኖክ ኃይሌ
መጋቢት 10 2014 ዓ.ም. ተጻፈ
ባሕር ዳር ኢትዮጵያ
ለተጨነቀች ነፍስ ዕረፍት የሆነው የእግዚአብሔር ቃል ለሁሉ ይዳረስ ዘንድ :: እኔም ለእናንተ ከሰበክሁ በኁዋላ የተጣልሁ እንዳልሆን ስለ እኔ ጸልዩ! "ለሚሰሙት ጸጋን ይሰጥ ዘንድ፥ እንደሚያስፈልግ ለማነጽ የሚጠቅም ማናቸውም በጎ ቃል እንጂ ክፉ ቃል ከአፋችሁ ከቶ አይውጣ" (ኤፌ 4:29)
ክርስቲያን ነህ?
ወዳጄ ሆይ !
እንኪያስ ክርስቶስ የሰጠህን ስጦታ ላልተፈለገ ግብር (ሥራ ) አታውለው
💠እጅን የሰጠህ እንድትሰርቅበት ሳይሆን
ትእዛዛቱን እንድትፈጽምበት :
በጎ ምግባርን እንድትሠራበት
ለጸሎት እንድትነሳበት
የወደቁትን እንድታነሣበት ነው ።
ጆሮን የሰጠህ ተርታ ወሬ እንድትማበት ሳይሆን
ቃሉን እንድታዳምጥበት ነው
አንደበትን የሰጠህ እንድትሰድብበትና እንድትረግምበት ሳይሆን
እንድትዘምርበት
እንድታመሰግንበት
እንድትመክርበት ነው።
እግርን የሰጠህ ወደ ክፋት ሳይሆን
ወደ በጎ ሥራ እንድትፋጠንበት ነው ።
ሆድን የሰጠህ ለመብል ሳይሆን ጥበብን እንድትማርበት ነው ።
ፈቲውን የሰጠህ እንድታመነዝርበትና እንድትዳራበት ሳይሆን ልጆችን ትወልድበት ዘንድ ነው ።
ልቡናን የሰጠህ ሰዎችን እንድትወቅስበት ሳይሆን
እውነትን ታውቅበት ዘንድ ነው ።
ገንዘብና ጉልበትን የሰጠን
ሰማያዊ ቤታችንን እንድንሠራበት ነው
እንኪያስ የክርስቶስን ስጦታ በአግባቡ ተጠቀምበት
ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቂ
/channel/dnhayilemikael
እየጦሙ አለመጦም
ተወዳጆች ሆይ ! እየጦሙ የጦምን ፍሬ ጻማ የማያገኙበት ሁኔታ እንዳለ ታውቁ ዘንድ እወዳለሁ
ይህስ እንደ ምን ነው ያላችሁኝ እንደሆነም :-
💠ከምግበ ሥጋ ተከልክለው ሳለ ከምግበ ኃጢአት ያልተከለከልን እንደሆነ
💠ከጥሉላት ርቀን ሳለ ነዳያንን ያልጎበኘን እንደ ሆነ
💠ወይን ከመጠጣት ታቅበን ሳለ በክፋ መሻት ከመስከር ያልራቅን እንደ ሆነ
💠ጀምበር እስክትጠልቅ ድረስ ከእህል ከውኃ ርቀን ሳለ በዓይናችን መልካም ያልሆኑ ትእይንቶችን ከማየት ያልጦምን እንደ ሆነ ነው ብዬ በእውነት ያለ ሐሰት እነግራችኋለሁ ።
✝️ስለዚህም እየጦሙ አለመጦም እንዳለ እወቁ : ተረዱም።
/channel/dnhayilemikael
†
🕊 [ ጾም ] 🕊
▬▬▬▬▬▬▬▬▬▬▬▬▬
[ ሦስት ነገሮችን ! ]
" በጾም ሰዓታችሁ ጊዜም ይኹን በሌላ ጊዜ ሦስት ነገሮችን በሕሊናችሁ ትይዙ ዘንድ እንመክራችኋለን፡፡
እነርሱም ክፉ ከመናገር መከልከልን ፣ ማንንም ሰው እንደጠላት ከማየት መቆጠብንና እንደልምድ አድርጋችሁ ከያዛችሁት መሐላ ትርቁ ዘንድ !
በአጨዳ ላይ ያለ ገበሬ እህሉን ከማሳው በአንዴ እንደማይሰበስብ ነገር ግን በጥቂት በጥቂቱ እንደሚሰበስብ ኹሉ እኛም እነዚህን ምክሮች ተግባራዊ በማድረግ በዚህ የጾም ወቅት ልንለማመዳቸው እና መልካም ልምዶቻችን ልናደርጋቸው ይገባናል፡፡
እንዲህ በማድረጋችንም በቀላሉ መንፈሳዊ ጥበብን ገንዘብ ማድረግ ይቻለናል፡፡ በዚህም ዓለም ሳለን መልካም ተስፋ ያለውን አዝመራ እናፈራለን። በሚመጣውም ዓለም በክርስቶስ ፊት ያለፍርሐት በደስታ ተሞልተን እንድንቆም ይረዱናል፡፡ ለዚህ የሚያበቃንን ጸጋ አግኝተን የክብሩ ወራሾች ያድርገን፡፡ " †
[ ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ ]
† † †
💖 🕊 💖
የእግዚአብሔርን ፈቃድ ልትረዳ የምትችለው ሁልጊዜ አንተ በምትፈልገው መንገድ ብቻ እንዲሠራ ባለመጠበቅ ነው። አንዳንዴ በአንተ እና በአምላክህ ሐሳብ መካከል የሰማይና የምድር ያህል ልዩነት ሊኖር ይችላል። ራሱ ባለቤቱም "ሰማይ ከምድር ከፍ እንደሚል፥ እንዲሁ መንገዴ ከመንገዳችሁ አሳቤም ከአሳባችሁ ከፍ ያለ ነው” ብሎናል።(ኢሳ 55፥9)
"ፈቃድህ ይሁን" ብለህ ከጸለይህ በኋላ "የምትፈልገውን ብቻ በመጠባበቅ ፈጣሪህን የፈቃድህ አገልጋይ አታድርገው። በጸሎትህ አምላክ የሚወደውን ወይም ፈቃዱን ማወቅ ከፈለግህ "አንተ የምትወደውን እንደ ብቸኛ መልስ አትጠባበቅ።
#10_የነፍስ_ጉርሻዎች_ከቅዱስ_ዮሐንስ_አፈወርቅ
#አንድ
"ቃላቶችህ ምንም ያህል ትክክል ቢሆኑም በቁጣ ስትናገር ሁሉንም ነገር ታበላሻለህ።"
#ሁለት
"ብል ልብስን እንደሚበላው ሰውንም ቅናት ይበዋል።"
#ሶስት
"እግዚአብሔር የሚጠይቀው ጥቂት፣ የሚሰጠው ብዙ ነው"
#አራት
"እያንዳንዱ ሰው የህይወቱ ሠዓሊ እና ቀራፂ ነው።"
#አምስት
"ባለጠጋ ብዙ ያለው ሳይሆን ብዙ የሚሰጥ ነው።"
#ስድስት
“ምሕረት አምላክን ይመስላል ሰይጣንንም ያሳዝነዋል።"
#ሰባት
" ኃጢአት ስትሠራ እንጂ ንስሐ ስትገባ አትፈር"
#ስምንት
"ለምን በትንንሽ ነገሮች መደሰትን አትማርም - በጣም ብዙ ናቸው።"
#ዘጠኝ
"ጸሎት የጭንቀት ሁሉ መሸሸጊያ፣የደስታ መሠረት፣ ከሐዘን መከለያ ናት። "
#አስር
"ክርስቶስን በቤተ ክርስቲያን ደጃፍ ላይ ባለው ነዳይ ውስጥ ማግኘት ካልቻላችሁ፣ በቤተመቅደስ ውስጥ አታገኙትም።"
ቴሌግራም ቻናል ተቀላቀሉ
╭═══•|❀:✧๑♡๑✧❀|: ═══╮
የመሰረተ ተዋሕዶ ሰንበት ትምህርት ቤት መገናኛ ብዙሃን
➡️ መሰረተ ሚዲያ
👇👇👇👇👇👇👇👇👇👇
ቻነሉን share በማድረግ
መሠረተ ሚዲያ አብረን እናሳድግ
👇👇👇👇👇👇👇👇
የቴሌግራም አድራሻ ⤵️ ⤵️ ⤵️ ⬇️═/channel/Meseretemedia
ቤተክርስቲያንን በሁለት መንገድ ማወቃችንን እናረጋግጥ።
👇👇👇👇👇👇👇👇👇
እንደ አሕዛብ ጠላቷ እንዳንሆን 👉በትምህርት_እንወቃት፤
እንደ ፈሪሳውያን እንዳንሆን👉 በኑሮ_እንወቃት።
ለሥርዓቷ ታማኝ እንሁን ፥
እኛ ወደ ሥርዓቷ እንደግ እንጅ ሥርዓቷ ወደ እኛ ፈቃድ እንዲወርድልን አንውደድ፤
ሰማያውይቷን ቤተክርሰቲያን ምድራዊት እንድትሆንልን አንፍቀድ። በቤተክርስቲያን መንፈሳዊ አንድነቶች ካልተሳተፍን ከቤተክርስቲያን አንድነት እየተለየን እንደሆነ እንወቅ። እነዚህም
👉ኪዳን ማስደረስ፥
👉ማስቀደስና
👉ንስሐ ገብቶ መቁረብ፥
👉 በምህላ ጸሎቶቿ
👉 በአዋጅ አጽዋማቷ መተባበር ናቸው።
ከቤት ከሚጸለይ አሥር ጸሎት ይልቅ በቤተክርስታያን የሚደረግ አንድ ጸሎት እንደሚበልጥ አውቀን በየቀኑ ወደ እርስዋ እንገሥግሥ። በሕይወታችን ሁሉ ቤተክርስቲያናዊ እንሁን!።
(ርዕሰ ሊቃውንት አባ ገብረኪዳን ካስተማሩት!)